የኢትዮጵያ ድርቅ
እሑድ፣ የካቲት 5 2009ኢትዮጵያ ስሟ በድርቅና እና ረሀብ መጠራት ከጀመረ ከ4 አሥርት ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል ። ረሃብ እና ድርቅ በኢትዮጵያ የሰው እና የእንሰሳት ህይወት ሲያጠፋ በርካታ ዜጎችንም የምግብ እርዳታ ጥገኛ ሲያደርግ ቆይቷል ። የሩቆቹን ትተን የቅርብ ጊዜውን ብናነሳ ከአንድ ዓመት በፊት በኢትዮጵያ በ50 ዓመት ታሪክ ታይቶ የማታውቅ የተባለ ከባድ ድርቅ 10.2 ሚሊዮን ህዝብዋን ለምግብ እጥረት ሲያጋለጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ እንሰሳትን ህይወትም አጥፍቷል ። ከአምናው ድርቅ ገና ያላገገመችው ኢትዮጵያ ዘንድሮ እንደገና በአዲስ ድርቅ ተመታለች ። በአሁኑ ድርቅ ከ5.6 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቸኳይ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው የኢትዮጵያ መንግሥት እና ዓለም ዓቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች አስታውቀዋል ። የአሁኑ ድርቅ ለምግብ እጥረት ያጋለጠው ሕዝብ ካለፈው ዓመቱ በመጠን ያነሰ ቢሆንም የብዙ እንሰሳትን ህይወት ማጥፋቱ ተገልጿል ። የኢትዮጵያ መንግሥት ችግሩን ለመቋቋም 47 ሚሊዮን ዶላር መመደቡን አስታውቆ ለዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ የ948 ሚሊዮን ዶላር የእርዳታ ጥሪ አቅርቧል ። የመኸር ዝናብ በማጠሩ ምክንያት ተከሰተ የተባለው ይህ ድርቅ ምን ያህል አሳሳቢ ነው ? ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ የሚገጥማትን ድርቅ ለመቋቋም የምትከተለው መንገድ እንዴት ይገመገማል ? በኢትዮጵያ ድርቅን በዘላቂነት መቋቋሚያ መፍትሄስ ይኖር ይሆን ? የዛሬው እንወያይ የሚያተኩርባቸው ጉዳዮች ናቸው ። በዚህ ላይ የሚወያዩ ሦስት እንግዶችን ጋብዘናል ። እነርሱም አቶ ደበበ ዘውዴ በኢትዮጵያ ብሔራዊ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ፣ ዶክተር አየለ ጉግሳ የምግብ ሳይንስ ባለሞያ ፣ እንዲሁም አቶ ግርማ ሰይፉ የቀድሞ የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ናቸው .። የድምጽ ማዕቀፉን በመጫን ሙሉውን ውይይት ማዳመጥ ይችላሉ ።
ኂሩት መለሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ