1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የኢትዮ ሱዳን የድንበር አካባቢ ባለሥልጣናት ውይይት

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 24 2015

ከአንስሳት ሰርቆትና ከሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ጋር በተያያዘ በሱዳንና ኢትዮጵያ አዋሳኝ አካባቢዎች ያለውን የሰላም መደፍረስ ሊያለዝብ ችላል የተባለ ውይይት ተካሄደ። በተካሄዱ ውይይቶች የአካባቢው የፀጥታ ሁኔታ እየተሸሻለ መሆኑ ተገልጿል።

Diskussionen zwischen Äthiopien und Sudan Grenzbeamten im Quara Amgara Region
ምስል፦ Quara Prosperity Party Office Head

የኢትዮ ሱዳን ድንበር

This browser does not support the audio element.

 

ሱዳንና ኢትዮጵያ በድንበር አካባቢ አልፎ አልፎ በሚፈጠሩ የተለያዩ ምክንያቶች ወደ አለመግባባት እየደረሱ በታጣቂዎች መካከል ግጭቶች እየተከሰቱ በየአካባቢዎቹ ነዋሪዎች ላይ ማኅበራዊ ችግሮች ይፈጠራሉ። በተለይ ከእንስሳት ስርቆት ጋር በተያያዘ በሁለቱ አጎራባች  ወረዳዎች መካከል ግጭቶች ሲነሱ ቆይተዋል። እነኝህን ችግሮች ለማስወገድና ተጠያቂ የሆኑ ግለሰቦችን አሳልፎ መስጠት የሚያስችልና ከሁለቱም ወገን የተሰረቁ እንስሳት ወደየአካባቢዎቹ እንዲመለሱ የሚያደርጉ ውይይቶች በአካባቢ አስተዳደሮች መካከል ሲካሄድ እንደነበርና ሰሞኑንም የዚያው ተከታይ የሆነ ውይይት በቋራ ወረዳ ነፍስ ገበያ ቁጥር 4 መካሄዱን በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር ዞን  የቋራ  ወረዳ ብልፅግና ፓርቲ አመልክቷል።

የፓርቲው ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደሳለኝ ሞገስ ለዶቼ ቬሌ በስልክ እንደተናገሩት፣ በተከታታይ የተደረጉ ውይይቶች ውጤት አስመዝግበዋል፣ ከእኛ የተዘረፉ እንስሳት ተመልሰዋል ከእነርሱም የተወሰዱ እንስሳት ተመልሰዋል ብለዋል። ከአንድ ወር በኋላ ውይይቱን ወደ ዞን ደረጃ ለማሳደግ እቅድ መያዙን የሚናገሩት አቶ ደሳለኝ፣ በተገኙ ውጤቶች ኅብረተሰቡ እፎይታ ማግኘቱን አመልክተዋል።

የምዕራብ ጎንደር ዞን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊ አቶ ፋንታሁን ቢሆነኝ በበኩላቸው ኢትዮጵያና ሱዳን የረጅም ጊዜ ወዳጆች መሆናቸውን አስታውሰው በየጊዜው የሚደረጉ ውይይቶች የሁለቱን ሃገራት ህዝቦች የቆየ ታሪካዊ ትስስር ለማጠናከር እና ሰላማዊ ግንኙነቱም የጎላ እንዲሆን ያለመ መሆኑን ለዶይቼ ቬሌ አብራርተዋል።

የኢትዮ ሱዳን የድንበር አካባቢ ባለሥልጣናት ውይይት ምስል፦ Quara Prosperity Party Office Head

አገራዊ የሆኑና ከፍ ያሉ ጉዳዮች በፌደራል ደረጃ የሚታዩ እንደሆኑ ያመለከቱት አቶ ፋንታሁን «በዞንና በወረዳ ደረጃ የሚፈቱ ችግሮችን እየፈታን ነው»ም ብለዋል። በጥቅምት 24/2013 ዓ ም  የተከሰተውን የሰሜን ጦርነት  ተከትሎ የሱዳን ጦር በተለያዩ የምዕራብ ጎንደር አካባቢዎች በግብርና ዘርፍ በተሰማሩ ባለሀብቶች ላይ ጥቃት ከፍቶ ነበር፤ በሰኔ 2014 ዓ ም ደግሞ የሱዳን መንግሥት «ሰባት ወታደሮቼ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ተገድለውብኛል» በሚል፣ ሁለቱ አገሮች የይገባኛል ጥያቄ በሚያቀርቡበት የአልፋሽጋ አካባቢ የሱዳን ጦር ጥቃት ፈፅሞ ነበር። በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግሥት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ወታደሮቹን እንዳልገደለ መግለጹ ይታወሳል።

 ዓለምነው መኮንን 

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW