የኢትዮ ጅቡቲ የባቡር መስመር
ሰኞ፣ ታኅሣሥ 5 2013
ከአዲስ አበባ ጅቡቲ የተዘረጋው አዲሱ የባቡር መጓጓዣ አገልግሎት በተለያዩ ጊዜያት በሚያጋጥመው ስርቆት እና የባቡር እገታ ሳቢያ ከፍተኛ ኪሳራ እየደረሰበት መሆኑን አስታወቀ። በሌላ በኩል ባቡሩ በሚያልፍበት መስመር ላለው ኅብረተሰብ የሚፈለገውን ዓይነት ጥቅም እየሰጠ አይደለም ሲሉ በሶማሌ ክልል የሚገኙ ነዋሪዎች እና ኃላፊዎች ቅሬታ አቅርበዋል። በኢትዮ - ጅቡቲ ባቡር መጓጓዣ አ.ማ የባቡር ደህንነት ኃላፊ ኢንጅነር ጥበቡ ተረፈ ለDW በሰጡት መግለጫ በተቋሙ ንብረት ላይ የሚፈፀም ስርቆት፣ በእንስሳት ላይ የሚደርስ አደጋ እና ይህንኑ ተከትሎ ከካሳ ጥያቄ ጋር በተያያዘ የሚፈፀም የባቡር ህገታ ሳቢያ ከፍተኛ ኪሳራ እየደረሰ ነው ብለዋል። በአንጻሩ የባቡር መጓጓዣ መስመሩ መሰረተ ልማት ላይ እየደረሱ ያሉ ችግሮች ላይ ለመነጋገር በድሬደዋ በተካሄደው የውይይት መድረክ ተሳታፊ የሆኑት አቶ ሙሴ ሊባህ የባቡር መጓጓዣ ለአካባቢው ኅብረተሰብ የመጓጓዣ ችግር የፈየደው ነገር የለም ሲሉ ቅሬታ አቅርበዋል። በውይይቱ የባቡር መጓጓዣ ላይ እያጋጠሙ ላሉ ችግሮች በተለይ ኅብረተሰቡ የባለቤትነት ስሜቱ ዝቅተኛ መሆን በምክንያትነት ተነስቷል። አገልግሎቱ በተዘረጋበት መስመር በቂ መሻገርያ አለመኖር ፣ በሁሉም ዘርፍ የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እና ሌሎችም አሉ ያላቸው ችግሮች ተነስረተተዋል። በኅብረተሰቡ የተነሱ ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት ጥረት እንደሚደረግ በኢትዮ - ጅቡቲ ባቡር መጓጓዣ አ.ማ ዋና ዳይሬክተር ኢ/ር ጥላሁን ሳርካ አስረድተዋል። የመጓጓዣ አገልግሎቱ ከተጀመረ አንስቶ 27 ሰዎች ሲሞቱ 11 የሚሆኑት ከባድ አካል ጉዳት መድረሱን፤ 960 አንድ ስርቆት ሲፈፀም 163 ጊዜ ባቡሩን የማገት ድርጊት መፈፀሙን ከተቋሙ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
መሳይ ተክሉ
ሸዋዬ ለገሠ
እሸቴ በቀለ