የኢድ አልአድሀ አከባበር በአዲስ አበባ እና በሳዉዲ
ዓርብ፣ ነሐሴ 26 2009ማስታወቂያ
በዘንድሮዉ የሐጂ ሃይማኖታዊ ጉዞ እና ጸሎት ወደ ሰባት ሺህ የሚሆኑ ኢትዮጵያዉያን መሳተፋቸዉን ጄዳ የሚገኘዉ ጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ ለዶቼ ቬለ ገልጿል። በዓሉን በዚያዉ ሳዉድ አረቢያ የሚያከብሩ ኢትዮጵያዉያን ለዶቼ ቬለ እንደገለፁት የሳዉዲ መንግሥት በዉጭ ዜጎች ላይ የጣለዉ የነፍስ ወከፍ ግብር፣ የትምህርት ቤት ክፍያ እና ሌሎች ወጪዎች የበዓል ድባባቸዉ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳርፏል። የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት በውጭ ሀገር ዜጎች እና በቤተሰቦቻቸው ላይ በጣለው የነፍስ ወከፍ ክፍያ የተነሳ አብዛኞቹ ኢትዮጵያዊያን ልጆቻቸውን ወደ ሀገራቸዉ እየላኩ ነው፡፡ ይሁንና የኑሮን ውጣ ውረዱን ተቋቁሞ በዓሉን በተረጋጋ መንፈስ ማክበር እንደሚያስፈልግ አንድ የሃይማኖት አባት መክረዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለም። ኢትዮጵያ ዉስጥም በተለይ በአዲስ አበባ ስታድዮም ፀጥታዉ በተጠበቀ መልኩ በዓሉ ተከብሯል። በበዓሉ ላይ የተገኙ የሃይማኖቱ መሪዎች እና የመንግሥት ኃላፊዎች በሀገሪቱ የመቻቻል ባህል እንዲጎለብት ጥሪ አቅርበዋል።
ዮሐንስ ገ/እግዚአብሔር/ነብዩ ሲራክ/ ስለሺ ሽብሩ
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ