የኤሌክትሪክ መሐንዲሱ አቶ ታምሩ በሻህ
ረቡዕ፣ ሰኔ 19 2005 ውስጥም በሰለጠኑበትና ብዙ ልምድ ባካበቱበት ሞያ አማካሪ ድርጅት አላቸው ። አቶ ታምሩ በሻህ የዛሬ 43 ዓመት የነፃ ትምህርት እድል አግኝተው ወደ ጀርመን ከመጡት 14 ኢትዮጵያውያን አንዱ ነበሩ ። ጀርመን ከመምጣታቸው በፊት በዚያን ጊዜው አጠራር በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ የ1ኛ ዓመት የምህንድስና ተማሪ ነበሩ ። ትምህርቱ የሚሰጠው በጀርመንኛ ስለሆነ ለ3 ወራት ቋንቋ ተምረው የነፃ ትምህርት እድል ባገኙበት በባቫርያው የኮቡርጉ ኮሌጅ ገብተው ዋናውን ትምህርት ከመጀመራቸው በፊት የስራ ላይ ስልጠና ወስደዋል ።
አቶ ታምሩ ትምህርታቸውን ከጨረሱ በኋላ በሞያቸው ስራ ማግኘቱ ጊዜ አልወሰደባቸውም ። በተቀጠሩባቸው መስሪያ ቤቶችም በተለያዩ የሃላፊነት ደረጃዎች ሰርተዋል ።
አቶ ታምሩ በተማሪነታቸው ዘመንም ሆነ ስራ ከያዙ ወዲህ ፣ማንኛውም የውጭ ዜጋ ጀርመን ውስጥ ሊያጋጥመው ከሚችል አድልዎና መገለል አላመለጡም ።
ይሁንና በበኩላቸው ተፅእኖዎቹን በራስ በመተማመን መንፈስና በጥንካሬ ለመቋቋም እንደቻሉ ነው የሚናገሩት ። በዚህ ረገድ በስራ ቦታ የደረሰባቸውን አድልዎ የተቋቋሙበትን መንገድ በምሳሌነት ያነሳሉ ።
ከፍተኛ ትምህርታቸውን በተከታተሉበት በጀርመን በታዋቂ የቴሌኮምኒኬሽን ድርጅቶች የሰሩት አቶ ታምሩ በሻህ ከ 13 ዓመታት በኋላ ፊታቸውን ወደ ግል ስራ አዞሩ ። እጎአ በ1999 ለአንድ ስብሰባ አሜሪካን በሄዱበት አጋጣሚ የተዋወቁት አሜሪካዊ ኢትዮጵያ ውስጥ በግል ዘርፍ ቢሰማሩ ብዙ እድል እንዳለ ሲያነሳሳቸው በተለይ በቴሌኮሚንኬሽን ዘርፍ ለመስራት አስበው ይህ የማይቻል መሆኑን ካደረሱበት በኋላ በኃይል መስክ ለመሰማራት አቀዱ ።
አቶ ታምሩ ኢትዮጵያ ውስጥ ከመሰረቱት ድርጅት በተጨማሪ ፣ ጀርመን ውስጥ ባቋቋሙት አማካሪ ድርጅታቸው አማካይነት ኢትዮጵያ ውስጥ ፕሮጀክት ከሚያካሂዱ የጀርመን ድርጅቶች ጋርም እየሰሩ ነው ።
ምንም እንኳን የአቶ ታምሩ ሃሳብ ተሳክቶ ኢትዮጵያ ውስጥ የራሳቸውን ድርጅት መመስረት ቢችሉም ሥራው ግን ባሰቡት ፍጥነት መጓዝ አልቻለም ። በተለይ እጎአ በ2008 ያጋጠማቸው ችግር ብዙ ስራዎቻቸውን ወደ ኋላ አጓቷል ።
የፀሐይ ብርሃንን በኤሌክትሪክ ሐይል ምንጭነት መጠቀሙ ለኢትዮጵያ ጠቃሚ ቢሆንም ቱክኖሎጂው ግን ኢትዮጵያ ውስጥ እምብዛም ጥቅም ላይ አይውልም ። አቶ ታምሩ ምክንያቶቹን ያስረዳሉ ።
እንደ አቶ ታምሩ ኢትዮጵያ ከፀሀይ ብርሃንም ሆነ ከሌሎች አማራጭ የኃይል ምንጮች ይበልጥ ተጠቃሚ የምትሆነበት መንገድ ካልተፈለገ በስተቀር ከኋላ ቀርነት ልትላቀቅ አትችልም ።
አቶ ታምሩ በሻህ ባለትዳርና ከጀርመናዊት ባለቤታቸው ያፈሯቸው የ3 ልጆች አባት ናቸው ።
ሂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ