የኦሮሚያ ም/ቤት አባላት ያለመከሰስ መብት መነሳት
ዓርብ፣ ሰኔ 3 2008ያለመከሰስ መብታቸው የተነሳውም በምክትል ፕሬዚደንት ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ ዘላለም ጀማነ እና የሱሉልታ ከተማ ምክትል ከንቲባ የነበሩት አቶ ዲሮ ደሜ ናቸዉ። አቶ ዲሮ ደሜ የሱሉልታ ከተማ ከንቲባ እና በምዕራብ ሸዋ ዞን ጀልዱ ወረዳ የጨፌ ተወካይ በነበሩት ወቅት ስልጣናቸውን <<ያለአግባብ በመጠቀም ስለተጠረጠሩ በፀረ-ሙስና ኮሚሽኑ ጥያቄ መሰረት የኦሮምያ ምክር ቤት ያለ መከሰስ መብታቸውን ማንሳቱን የመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
አቶ ዘላለም ጀማነም ሥልጣናቸውን አለአግባብ በመጠቀም ኃብት አካብተዋል ተብሏል። ተጠርጣሪው አቶ ዘላለም ጀማነ ዛሬ በብሾፍቱ ከተማ በቁጥጥር ስር መዋላቸዉ ተዘግቧል ። የመከሰስ መብቱ ሲነሳ አካሄዱ እንዴት እንደነበር በጫፌ ኦሮምያ የኮሙኒኬሸን እና እንፎርሜሸን ባለሙያ አቶ ሃብታሙ ደምሴ ለዶቼ ቬሌ አብራርተዋል፣ «አካሄዱ ችግር አልነበረዉም። በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄ የማቅረብ መብት ያላቸው እንደ መንግስት ተቋም ሁለት አካል ናቸው። አንዱ የፍትህት ቢሮ ስሆን ሌላዉ ደግሞ በህግም ተደንግጎ መብቱ ያለዉ የኦሮምያ የስነ ምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ነዉ። ለጨፌ ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ በምርመራም የተደረሰባቸዉ ጉዳዮችም ቀርበው፣ ተጨባጭ ማስረጃዎችም ከቀረቡ በኋላ የጨፌ አባላት ከተወያዩበት በኋላ ነዉ ያለመከሰስ መብታቸው መነሳት የቻለዉ።»
የጨፌ ኦሮሚያ ያለመከሰስ መብት የማነሳት ርምጃ ከተባለዉ የሙስና ክስ ይልቅ የፖለቲካ እንድምታ አለዉ የሚሉት ጉዳዩን በቅርበት የሚከታታሉት የፖለትካ ተንታኝ አቶ ገረሱ ቱፋ ናቸዉ። የነዚህ ግለሰቦች ያለመከሰስ መብት መነሳት ተደምሮ የክልሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት እና ምክትል ፕሬዝዳንት መነሳታቸዉ ለፓርቲዉም ሆነ ለማህበረሰቡ ብዙ እንድምታ እንዳለዉ ይናገራሉ። ዝርዝሩን ከድምጽ ዘገባዉ ያዳምጡ።
መርጋ ዮናስ
ሒሩት መለሰ