የኦፌኮ አመራሮች የፍርድ ቤት ዉሎ
ሰኞ፣ ጥር 28 2010ተከሳሾቹ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ማለትም አቶ ላማ ማጋርሳ፣ ዶክተር አብይ አህመድ፣ አባዱላ ጋመዳና ጫልቱ ናኒ ለየመከላከያ ምስክርነት እንድቀርቡ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4 ኛ ወንጀል ችሎት መጠየቃቸዉ ይታወሳል።
ይሁን እንጅ ጥር 3 ቀን 2010 ዓ.ም የፍርድ ቤቱ ዳኞች የተከሳቾች ጥያቄ ዉድቅ ማድረጋቸዉን ዘግበን ነበር። የፍርድ ቤቱ ርምጃ ተከትሎ ከላይ የተጠቀሱት የመጀመርያ አራቱ ተከሳሾች ባቀረቡት ተቃዉሞ «ፍርድ ቤትን ደፍራችኋል» በሚል የስድስት ወር ቅጣት መተላለፉንም በዘገባችን ጠቅሰናል።
ዛሬም ዳግም «ፍርድ ቤት ደፍራችኋል» በሚል የስድስት ወር ቅጣት መተላለፉን የተከሳሾቹ ጠበቃ አቶ ወንድሙ ኢብሳ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ሕገ-መንግስት አንቀፅ 19 ንዑስ አንቀስ ሁለት የተያዙ ሰዎች ያለመናገር መብት እንዳላቸዉ ይደነግጋል። ችሎቱ ወይም መርማሪ ፖሊሶች ለተከሳሾቹ ከፈለጉ ላለመናገር መብት እንዳላቸዉ፣ ከተናገሩ ደግሞ የሚናገሩት ሁሉ እንደ ማስረጃ እንደሚወሰድ በግልፅ መናገር አለባቸዉ ሲል የሐገሪቱ ሕገ መንግሥት ይደነግጋል።
የሕግ ባለሙያዉ አቶ በትሩ ዲባባ ለዶይቼ ቬሌ ይህንኑ ገልፀዋል። ሕገ-መንግስቱ ታሳሪዎቹ ያለመናገር መብት አላቸዉ ብሎ ከደነገገ፤ ዳኖች በምን የሕግ ማዕቀፍ ይህን አይነት ርምጃ መዉሰድ ይችላሉ? ለምለዉ ጥያቄ፣ የሕግ ባለሞያዉ በትሩ ዲባባ ሲገልፁ: «ጉዳያቸዉ በጠበቆች የተያዘላቸዉ ተከሳሾች ጠበቆቹ ስላሉ በግዴታ እናንተ ካልተናገራችሁ የሚባል ነገር የለም። በራሱ ገንዘብ እንኳን ጠበቃ ማስቆም ያልቻለ ተከሳሽ በመንግስት ወጭ ጠበቆች እንዲቆሙለት ይደረግና ጉዳያቸዉ በጠበቆቻቸዉ በኩል እንዲፈፀም ይደረጋል። ችሎትን ማክበር ያለ ጉዳይ ነዉ። ግን በአብዛኛዉን ግዜ የስድስት ወር ቅጣት ዉሳኔ የሚተላለፈዉ ተከሳሾች ችሎትን ስላላከበሩ ሳይሆን በዳኞቹ የግል ስሜት ላይ ተመስርተዉ ነዉ። ለምሳሌ ጠበቃ ቆሞለት እያለ ተከሳሹ ስላልተናገረ አልተናገርክም ብሎ መቅጣት፣ ሲናገር ደግሞ ተናገርክ ብሎ መቅጣት ተቃርኖ እንዳለዉ የሚያሳይ ነዉ»
አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ አቶ ጉርሜሳ አያኖ አቶ አዲሱ ቡላላ፣ አቶ ጌቱ ግርማ፣ አቶ በየነ ሩዳ፣ አቶ ተስፋይ ልባን እና አቶ ደረጀ መርጋ ላይ ዉሳኔ ለመስጠት ለየካትት 28 ቀን 2010 ቀጠሮ እንደተሰጣቸዉ አቶ ወንድሙ ኢብሳ ለዶይቼ ቬሌ ገልፀዋል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ