የኮንጎ መንግስት ከኤም 23 አማጺ ቡድን ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት ተፈራረመ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 12 2017
የኮንጎ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት በሩዋንዳ መንግስት እንደሚደገፍ ከሚነገርለት የኤም 23 አማጺ ቡድን ጋር የተኩስ አቁም ስምምነት ተፈራረመ ። የተኩስ አቁሙ ባለፈው ወር አሜሪካ ዋሽንግተን ውስጥ የተደረሰ የሰላም ስምምነት አካል ነው ተብሏል።
ሶስት ወራት የፈጀው እና አድካሚው የኮንጎ መንግስት እና የአማጺ ቡድኑ የተኩስ አቁም ድርድር በመጨረሻም ፍሬ አፍርቶ ዛሬ ቃጣር ዶሃ ውስጥ ተፈርሟል።
በስምምነቱ ሁለቱም ተፋላሚ ኃይሎች «በሃይል ተጨማሪ ቦታዎችን ለመያዝ የሚደረግ ሙከራን» ጨምሮ «ከጥላቻ ፕሮፖጋንዳ እንዲቆጠቡ እና ወደ ዘላቂ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያመሩ ቃል መግባታቸውን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
የአፍሪቃ ህብረት ስምምነቱን «ወሳኝ» ነው ሲል ፤ አሞካሽቶ በምስራቅ የዴሞክራሲያዊት ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ሰፊው የታላላቅ ሃይቆች አካባቢ ዘላቂ ሰላም ፣ ደህንነት እና መረጋጋትን ለማስፈን ለሚደረገው ጥረት ትልቅ ምዕራፍ ነው ብሏል።
ከሶስት አስርት አመታት በላይ ተንሰራፍቶ የቆየው የምስራቅ ኮንጎ ግጭት በሺዎች የሚቆጠሩትን ለሞት ፣ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩትን ደግሞ ከቤት ንብረታቸው አፈናቅሎ ብርቱ ሰብአዊ ቀውስ አስከትሏል።
በዚህ አመት ተጠናክሮ ብቅ ያለው የኤም 23 አማጺ ቡድን በማዕድን በበለጸገው ምስራቃዊ ኮንጎ ዴሞክራሲያዊት የጎማ ከተማን ጨምሮ የአካባቢውን በርካታ ከተሞች በቁጥጥሩ ስር ማዋሉን ተከትሎ በኮንጎ ዴሞክራሲያዊት ሪፐብሊክ እና በርዋንዳ መንግስታት መካከል ከፍተኛ ውጥረት እንዲገቡ አድርጓቸዋል።
ታምራት ዲንሳ
ዮሃንስ ገብረእግዚአብሄር