የወንዶገነት የተፈጥሮ ዉበት
እሑድ፣ ኅዳር 14 2012ከአዲስ አበባ በስተደቡብ አቅጣጫ በ275 ኪሜ ርቀት ላይ የሚኘው የወንዶገነት የመዝናኛ ስፍራ በ1949 ዓም በንጉስ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ልጅ ልዕልት ተናኘወርቅ እንደተቆረቆረ መረጃዎች ይጠቁማሉ። ጥቅጥቅ ባሉ ደኖችና በሰንሰለታማ ተራሮች የተከበበው የወንዶገነት የመዝናኛ ስፍራ በተፈጥሮ ሀብት ትሩፋቶቹ የታደለ ስለመሆኑ ያዩ ይመሰክሩለታል።
አገርበቀል ዛፎች ፣ ኩልል ያሉ ምንጮች ፣ ፍል ውሃዎችና አይነግቡ የሆኑ የባለቀለም አአዋፋት መኖሪያ መሆኑ ከተፈጥሮ በረከቶቹ መካከል የሚጠቀሱ ናቸው።
በወንዶገነት የመዝናኛ ስፍራ የጎብኚዎች አስተባባሪ አቶ ካሳዬ ገ/ህይወት በወቅቱ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ በመዝናኛ ስፍራው ያደረጉት ጉብኝት አካባቢው ዛሬ የሚታወቅበትን መጠሪያ ያገኘበትን አጋጣሚ መፍጠሩን ይገልጻሉ።
<< ንጉስ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ይህን ስፍራ በጎበኙበት ወቅት አካባቢው ምን ይባላል ብለው ሲጠየቁ ወንዶ ብለው ይነግሯቸዋል። እሳቸውም አካባቢው በደንና በሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች የታደለ መሆኑን አይተው በጣም ስለተደሰቱ ይሄ ምን ወንዶ ብቻ ገነትም ጭምር ነው ይላሉ ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ወንዶገነት ተበሎ እየተጠራ ይገኛል ። >> ይላሉ አስተባባሪው አቶ ካሳዬ ገ/ህይወት
በወንዶገነት የመዝናኛ ስፍራ ቀልብን ከሚገዙ መስህቦች መካከል ከከፍታ ቦታዎች በመነሳት ከአለቶች ጋር እየተጋጨ በመዝናኛ ስፍራው መሀል አቋርጦ የሚያልፈው ፏፏቴ አንዱ ነው። ከፏፏቴው ባሻገር ተንጣሎ የሚገኘው የመዋኛ ገንዳ ሙሉ በሙሉ በተመጠነ የተፈጥሮ ፍል ውሃ የተሞላ ነው ።
የወንዶገነት የመዝናኛ ስፍራ ከሌሎች የመዝናኛ ስፍራዎች የሚለይበት በመዝናኛ ስፍራው ይዞታ ውስጥ በአራት ቦታዎች ላይ ባለው የተፈጥሮ ፍል ውሃ ነው ። የተፈጥሮ ፍል ውሃው ከመዝናኛነት ባሻገር በርካቶች ለተለያዩ ህመሞች ፈውስን ለማግኘት እንደሚገለገሉበት የመዝናኛ ስፈራው የጎብኚዎች አስተባባሪ አቶ ካሳዬ ገ/ህይወት ይናገራሉ።
በአሁኑወቅት የመዝናኛ ስፍራ በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የሚናገሩት አቶ ካሳዬ ይሁንእንጂ አልፎ አልፎ በሚከሰተው የጸጥታ ችግር በተወሰነ ደረጃ የጎብኚዎች ቁጥር የመቀነስ አዝማሚያ ማሳየቱን ገልጸዋል።z
ሸዋንግዛዉ ወጋየሁ
አዜብ ታደሰ