የወጣቶች የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በደቡብ ወሎ
ረቡዕ፣ ሐምሌ 9 2017
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በኢትዮጵያ የክረምት መግባት ጋር ተያይዞ በወጣቶች የሚዘወተር ተግባር ሆኗል፡፡ በባለፈው አመት በ14 ተግባራት ዘንድሮ ደግሞ 17 ተግባራትን በመምረጥ በደቡብ ወሎ ዞን ብቻ ከ600 ሺ በላይ ወጣቶች ይህንን ተግባር ይፈፅማሉ፡፡ ወ/ሮ እናኒ ሰይድም የወጣቶች በጎነት ከከፈላቸው እናቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡
‹‹አባት የለኝም ፣ ወንድም የለኝም፣ አዎ ቤቴ ያፈስብኛል፤ የግድ ነው የት እሄዳለሁ ብየ እዚሁ እኖራለሁ፡፡ አላህን ይዤ እለምናለሁ፡፡ ቁሙልኝ፡፡››
ወጣቶች እራሳችንን ከመጥፎ ነገር በመጠበቅ ላስተማረን ማህበረሰብ የበኩላችንን አስተዋጽዖ የምናበረክትበት ዕድል አግኝተናል የሚለው ወጣት ሽመልስ አሊ የትላንትና እዳን በመክፈል እና ለነገ መልካም ስራ በማስቀመጥ ላይ ቁመናል ይላል፡፡ ‹‹ከበጎ ፈቃድ አገልግሎት ያገኘሁት እኔን የሚመስሉ ወጣቶችን እንደዚህ አይነት እድል የቀደመውን እዳ የምንከፍል ለወደፊቱ እቁብ እንደመጣል አድርገን ነው የወሰድነው፡፡››
የሰላም ግንባታ በበጎ ፈቃደኞች
በዋናነት በክረምት የበጎ ፈቃድ ተግባራት ላይ የሚሰራሙ ወጣቶች ለሠላም ትኩረት መስጠት አለባቸው የሚሉት አቶ መላኩ አምባው የበጎ ፈቃድ የወጣቶች አገልግሎትን የጦርነት እና የረሃብ ችግርን ሊቀይር የሚችል ተግባር ነው ይላሉ፡፡
‹‹በሀገራችን የሚታየው የሰላም እጦት ጦርነት፣ ችግር፣ ረሃብን መጥፎ ተግባራትን ሁሉ ሊቀይር የሚችል ትልቅ እና መልካም ተሞክሮ የምናገኝበት ነው፡፡››
615 ሺህ ወጣቶች ይሳተፋሉ
በደቡብ ወሎ ዞን በዘንድሮ የክረምት ወቅት 615ሺ ወጣቶች በክረምትየበጎ ፈቃድ አገልግሎትላይ ይሰማራሉ የሚሉት የደቡብ ወሎ ዞን ወጣቶች እና ስፖርት መምሪያ ሃላፊ አቶ ጀማል ሰይድ ናቸው፡፡
‹‹ወጣት 615ሺ እናሳትፋለን ከወጣት ውጭም ሌሎችበጎ ፈቃድ አገልግሎትየሚሰጡ 332 ሺ የህብረተሰብ ክፍሎች በጥቅሉ 948,386 የማህበረሰብ ክፍል ነው በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የሚሳተፈው፡፡››
በ17ተግባራቶች የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚሰጡ ወጣቶች በሰላም ግንባታ፣ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት እና በሌሎች አገልግሎቶች በመሳተፍ ከ800ሚሊየን ብር በላይ ሊወጣ የሚችልን የመንግስትን ወጭ ማዳን ይቻላል ተብሏል፡፡
834 ሚልየን ብር በበጎ ፈቃደኞች ይሸፈናል
‹‹አጠቃላይ በሚሰራው ስራ ወደ 1.8ሚሊየን የማህበረሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ መንግስት ሊያወጣ የሚችለውን 834ሚሊየን ብር ሀብት ከወጭ አድኗል፡፡ ወደ 17 ተግባራትን ተፈፃሚ ይሆናሉ፡፡››
አሁን በአማራ ክልል ካለው የሰላም ችግር ጋር ተያይዞም በዋነኝነት ወጣቶች ተሳታፊ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ አካባቢውም ወደቀደመ ሰላሙ እንዲመለስም የወጣቶች ተግባር ይሆናል ይላሉ አቶ ጀማል ሰይድ፡፡
‹‹እንደ ክልላችንም፣ እንደ ሀገርም የገጠመን የፀጥታ ችግር መንስኤው ቢታወቅም ዋናው ጉዳይና ተሳታፊው ወጣቱ ነው ወይም ደግሞ የወጣቱን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከዚህ ጋር ተያይዞም አቅደን በሰላም ግንባታ ዙሪያ ውይይት እያደረግን ነው፡፡ በጣም ብዙ ወጣቶች ጫካ ስለሆኑ እነርሱም በሀገር ሽማግሌ በሀይማኖት አባቶችም እየመከርን ይህንን ስራ እንዲያስተባብሩ እየሰራን ነው፡፡››
ኢሳያስ ገላው
ኂሩት መለሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ