የደቡብ ሱዳን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝደንት ሪየክ ማቻር ጠባቂ እስር ቤት መሞቱን ፓርቲያቸው ገለጸ
ቅዳሜ፣ መስከረም 10 2018
የደቡብ ሱዳን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝደንት የነበሩት ሪየክ ማቻር ጠባቂ በእስር ቤት መሞቱን ፓርቲያቸው አረጋገጠ። በእስር ላይ የሚገኙት ማቻር በደቡብ ሱዳን መንግሥት ግድያ፣ በመንግሥት ላይ ማሴር እና ሽብርተኝነት የሚሉትን ጨምሮ ስድስት ክሶች ተመስርቶባቸዋል።
የ72 ዓመቱ ፖለቲከኛ እና አብረዋቸው በእስር ላይ የሚገኙ አጋሮቻቸው በሀገር ክህደት፣ የመንግሥት እና የጦር ሠራዊቱን ንብረት ማውደም እና በሰብአዊነት ላይ ወንጀል መፈጸም የሚሉ ተጨማሪ ክሶች ቀርበውባቸዋል።
የደቡብ ሱዳን ፍትኅ ሚኒስቴር ባለፈው ሳምንት ክሱን ይፋ ካደረገ በኋላ ፕሬዝደንት ሳልቫ ኪር ሚያርዲት ምክትላቸው እና የፖለቲካ ተቀናቃኛቸውን ከሥልጣን አግደዋል። ምክትል ፕሬዝደንቱ እና ሌሎች ተጠርጣሪዎች በመጪው ሰኞ ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ የማቻር ጠበቆች አይ ራዲዮ ለተባለ የደቡብ ሱዳን መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።
ከሪየክ ማቻር ጠባቂዎች መካከል ሉካ ጋቶክ ኒዮን የተባለ ካፒቴን በጁባ በሚገኝ እስር ቤት ባለፈው ሐሙስ ሕይወቱ እንዳለፈ ፓርቲያቸው የደቡብ ሱዳን ሕዝብ ነፃ አውጪ ንቅናቄ - በተቃውሞ (SPLM-IO) ተጠባባቂ ሊቀ-መንበር ኦዬት ናትናኤል ፒየሪኖ ትላንት አርብ ባወጡት መግለጫ አረጋግጠዋል።
ሟቹ ወታደር በደቡብ ሱዳን መንግሥት ከታሠሩ 82 የማቻር ጠባቂዎች አንዱ ነበር። ሉካ ጋቶክ ኒዮን ሕይወቱ ያለፈው በጁባ በሚገኝ ወታደራዊ የጦር ሠፈር ውስጥ ሕክምና በመከልከሉ እንደሆነ የፓርቲው ተጠባባቂ ሊቀ-መንበር ወንጅለዋል።
የደቡብ ሱዳን ጦር በማቻር ጠባቂ አሟሟት ላይ ማብራሪያ ለመስጠት ቀጠሮ ይዞ የነበረ ቢሆንም የማቻር ፓርቲ ካወጣው መግለጫ በኋላ “ተዓማኒ መረጃ እስከሚሰበሰብ” በሚል ሰርዞታል።
አርታዒ ታምራት ዲንሳ