የሜርክል የኢትዮጵያ ጉብኝት
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 1 2009
ሜርክል በሃገሪቱ የተቃዉሞ ሰልፍ ሊፈቀድ ይገባል ፤ ፖሊስ የሚወስደዉ እርምጃም ተመጣጣኝ ሊሆን ይገባል ብለዋል። የመንግሥት ተቃዋሚዎች በሃገሪቱ ፖለቲካ ሊሳተፉ እንደሚገባም ተናግረዋል። መራሂተ መንግሥቷ ከቀትር በኋላ የአፍሪቃን ኅብረት በመጎብኘት በጀርመን መንግሥት ድጋፍ የተገነባውን የአፍሪቃ ኅብረት የሠላም እና የፀጥታ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት ሕንጻን መርቀዋል።
የጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል በመጪው የጎርጎሮሳዊው ዓመት በቡድን 20 ፕሬዝዳንትነታቸው ለአፍሪቃ ጉዳይ ቅድሚያ እንደሚሰጡ አስታወቁ ። ሜርክል ዛሬ አዲስ አበባ በሚገኘው የአፍሪቃ ህብረት ፅህፈት ቤት ተገኝተው ባሰሙት ንግግር በበጎርጎሮሳዊው 2017 አጋማሽ ላይ የኢንዱስትሪዎች ተወካዮች እና ዓለም ዓቀፍ ድርጅቶች የሚካፈሉበት አፍሪቃ ላይ ያተኮረ ጉባኤ በርሊን ውስጥ እንደሚካሄድም ተናግረዋል። ለአፍሪቃ ዘላቂ እድገት እና የሥራ እድል ፈጠራ በአፍሪቃ የግል ውረታ እንዲጠናከር የሀገራቸው ፍላጎት መሆኑንም ሜርክል ገልፀዋል ። በክፍለ ዓለሙ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት እና ሙያዊ ሥልጠናዎችንም ማሻሻል አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል ።ሜርክል በንግግራቸው የአፍሪቃ ሀገራት ጽንፈኛ ሙስሊም ተዋጊዎችን እና ህገ ወጥ ስደትን ከአሁኑ በበለጠ እንዲዋጉም ጠይቀዋል ። የአሸባሪዎችን እንቅስቃሴ ለመግታትም ዴሞክራሲያዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ተሃድሶዎችን ተግባራዊ እንዲያደርጉም አሳስበዋል ።ህብረቱ የሊቢያውን ግጭት ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ውስጥም እንዲሳተፍ ጠይቀዋል ። ሜርክል በዛሬው የአፍሪቃ ህብረት ጉብኝታቸው በጀርመን መንግሥት ድጋፍ የተገነባውን የአፍሪቃ ህብረት የሰላም እና የፀጥታ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት ህንጻን መርቀዋል ።
ዮኃንስ ገ/እግዚአብሔር
ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ