1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጀርመን-አፍሪቃ የሐይል ምንጭ ትብብር

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 3 2005

የአፍሪቃ ክበብ፥ አፍሪካ-ፈርአይንስ-በጀርመንኛዉ የበላይ ሐላፊ ክርስቶፍ ካኔንጊይሰር እንደሚሉት ዛሬ አፍሪቃን የሚሹት፥ ከብራዚል-እስከ አዉሮጳ፥ ከቱርክ እስከ ቻይና፥ ከሩሲያ-እስከ ሰሜን አሜሪካ ከሕንድ እስከ አረቦች ብዙ ናቸዉ።አፍሪቃዉያንም ብዙዎችን ይጋብዛሉ።

Christoph Kannengießer, Hauptgeschäftsführer des Afrika-Vereins der deutschen Wirtschaft
ካኔንጊይሰርምስል Antonio Cascais

የጀርመንና የአፍሪቃ ሐገራት በሐይል ምንጩ መስክ በሚያደርጉት ትብብርና የንግድ ልዉዉጥ ላይ ሰሞኑን የመከረዉ ስብሰባ ትናንት ማምሻዉን ተጠናቅቋል።ካለፈዉ ዕሁድ ጀምሮ ሐምቡርግ እና ሐኖፈር ዉስጥ ተስይሞ የነበረዉ ስብሰባ ሁለቱ ወገኖች በሐይል ምንጩ መስክ ያላቸዉን ግንኙነት ለማጠናከር ይረዳሉ የተባሉ ዉይይቶችና ጥናታዊ ማብራሪዎች ቀርበዉበት ነበር።«የጀርመን-አፍሪቃ የሐይል መድረክ» የተሰኘዉ ማሕበር የሁለቱ ወገኖች ተወካዮች የሚነጋገሩበትን ስብሰባ ሲያዘጋጅ የዘንድሮዉ ሰባተኛዉ ነዉ።
«ብዙ አፍሪቃዉያን በገበያዉ እንድንሳተፍ፥ እንደ ብራዚል፥ ሕንድ፥ ቱርክን ከመሳሰሉት በማደግ ላይ ከሚገኙት ሐገራት ጋር እንድንፎካከር እየገፋፉን ነዉ።የጀርመን ምጣኔ ሐብት የአፍሪቃ ማሕበረም፥ የጀርመን ኩባንዮች ይሕን እድል አዉቀዉ እንዲጠቀሙበት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ነዉ።»
እስከ ትናንት ድረስ ሐቡርግና ሐኖፈር የመከረዉ አይነት ስብሰባንና ዉይይቶችን መጥራትና ማዘጋጀት ከማሕበሩ ጥረቶች አንዱ ነዉ።
በ1933 (እ.ጎ.አ) የሐምቡርግ-ብሬሜን የአፍሪቃ ክበብ የተሰኘዉ ማሕበር ሲመሠረት አብዛኞቹ የአሪቃ ሐገራት በአዉሮጳ ቅኝ አገዛዝ ይማቅቁ ነበር።ያኔ-እንደዘበት የተመሠረተዉ ማሕበር ዛሬ-በብዙ መስክ፥ በርካታ ቅርንጫፎችን የያዘ፥ ከመላዉ ጀርመን በመላዉ አፍሪቃ የሚሠሩ ድርጅትና ተቋማትን ያሰባሰበ ማሕበር ነዉ።
ከቅርንጫፎቹ አንዱበጀርመንኛዉ፥ዶች-አፍሪካኒሸ ኢነርጊፎሩም፥ (በጥሬዉ የጀርመን-አፍሪቃ የሐይል መድረክ ብንለዉ ያስኬዳል)፥ በሐይል ምንጭ መስክ የተሰማሩና ለመሰማራት የሚሹ የአፍሪቃና የጀርመን ኩባንዮች ተጠሪዎች፥ የንግድ ድርጅት ሐላፊዎች፥ ፖለቲከኞች፥ ባለሙያዎችና ምሕራንን ሲያወያይ የዘንድሮዉ ሰባተኛቸዉ ነዉ።
ከጀርመን-የመኪና አምራች እስከ አፍሪቃ ነዳጅ አምራች ኩባንዮች፥ ከጀርመን የኤሌክትሪክ ሐይል ቁሳቁስ ሠሪ ፋብሪካዎች፥ እስከ አፍሪቃ ጋዝ አቅራቢዎች፥ከጀርመን የነፋስ፥ የፀሀይ ሐይል ማመንጫ መዘዉር ሰሪ ተቋማት እስከ አፍሪቃዉያን ተጠቃሚዎች የሚገኙ ድርጅቶችና፥ ተቋማት ተወክለዋል።
ጀርመኖች በጣም የሚፈልጓቸዉ ግን ካኔንጊይሰር እንደሚሉት ተወዳጁ ሐይል ያላቸዉ-ሐያል ወይም ቱጃር የአፍሪቃ ሐገራት ናቸዉ።«ከጀርመን ኩባንዮች ትኩረት አኳያ ሲታይ፥ ደቡብ አፍሪቃ፥ ናይጄሪያ፥ አንጎላ፥ ኬንያ እና የመግሪብ አካባቢ ሐገራት ትልቅ ተፈላጊነት አላቸዉ።»
ይሕ ማለት ግን ሌሎቹ የአፍሪቃ ሐገራት «ከሌለሕ የለሕም» ተብለዉ ይተዋሉ ማለት አይደለም። እንዲያዉም ካኔንጊሰር እንደሚሉት ደረጃዉ ይለያይ እንጂ የሐይል ምንጭ የሌለዉ ወይም ሐይል የማይሻ የአፍሪቃ ሐገር የለም።
«ይሁንና ብዙ ኩባንዮች ሌሎች ትናንሽ ገበያዎችን እያጤኑ፥ ጥሩ ግንኙነት እየመሠረቱና እየተሳካላቸዉም ነዉ።በመሠረቱ የሐይል ጉዳይ መላዉ አሕጉሪቱን የሚመለከት ነዉ።የሕዝቡን የኤሌክትሪክ ሐይል ፍላጎት በተመለከተ አፍሪቃ ከፍተኛ እጥረት ያለባት አሐጉር ናት።ከአምሥት መቶ እስከ ስድስት መቶ ሚሊዮን የሚገመት አፍሪቃዊ አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ሐይል አያገኝም።ሥለዚሕ የሐይል ጥያቄ ሐምሳ አራቱም የአፍሪቃ ሐገራት በሙሉ የሚመለከት ነዉ።»

የአፍሪቃ ሕብረት በቅርቡ ያወጣዉ ሰነድ ደግሞ አፍሪቃ ዉስጥ በተለይ በሐይሉ መስክ ለመስራት ለሚፈልጉ ኩባኖዮች ትልቅ ገበያ ከፋች ነዉ።«የአፍሪቃ ሕብረት እስከ ሁለት ሺሕ አርባ ድረስ ማለት በሚቀጥሉት ሐያ-አምስት ዓመታት ዉስጥ የአሐጉሪቱን የኤሌክትሪክ ሐይል አቅርቦት በአምስት እጥፍ ለማሳደግ የቀየሰዉ ፕሮጄክት አለ።መላዉ ዓለም ከሚሳተፍበት ከዚሕ ገበያ የጀርመንን ድርሻ ይሆናል ብለን የምንገምተዉን ብንወስድ የሰማንያ ቢሊዮን ዩሮ ገበያ የማግኘት እድል ይኖረዋል።ይሕ ደግሞ የሚቻል ነዉ።»
ለመቻል ግን የጀርመኖቹ ወይም የሌሎቹ የዉጪ ባለሐብቶች ፍላጎት ብቻዉን በቂ አይደለም። የአፍሪቃ መንግሥታት የየሐገራቸዉን ሠላምና ፀጥታ መጀመሪያ ራሳቸዉ ማክበር፥ ቀጥሎ ከሎች አዋኪዎች መጠበቅ፥ ከመዋለ ንዋዩ ፍሰት ሐገርና ሕዝብ እንዲጠቀም ማድረግ፥ ግልፅ ሕግ ማዉጣትና ለየጎቻቸዉ መገዛት እና ሙስናን ማጥፋት ግፍ ይላቸዋል።

አፍሪቃ -የፀሐይ ሐይልምስል DW
አፍሪቃ -ሐይልምስል www.BilderBox.com
ሐምቡርግ-ስብሰባዉምስል DW/A. Cascais



አንቶኒዮ ካስካሲየስ/ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ




ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW