የጋራ ማስተር ፕላንና ያስከተለዉ ቀዉስ
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 12 2008የእትዮጵያ መንግስት ማሰተር ፕላኑ ለልማት ጠቃሚ ነዉ እያለ ቢከራከሪም ተቃውሞዉን የሚያሰሙት ደግሞ ይህ የጋራ ማስተር ፕላን ልማትን ተገን በማድርግ በ37 ከተሞችና 17 ወረዳዎች ዉስጥ የሚገኙትን ገበሬዎችንና ነዋሪዎችን ከአከባቢያቸዉ የሚያፈናቅል ነዉ ስሉ ይከራከራሉ። ገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ላለፉት 24 ዓመታት በልማት ስም ሰዎችን ያለተገቢ ካሳ ከቦታቸዉ ማፈናቀል ከዛም አልፎ የሰዎቹን የቋንቋ እና የባህል አኗኗር ጥያቄ ዉስጥ እየከተተ ነዉ ሲሉ የሚተቹም አሉ። ይህ የጋራ ማስተር ፕላንም በኢትዮጵያ ህገመንግስት መሠረት ፤ የኦሮሚያ ክልል በከተሞች ላይ ያለዉን ልዩ ጥቅም ፣ የማህበራዊ ና ኢኮኖሚያዊ መብቶችን፣ ህብረተሰቡ በልማት እንቅስቃሴዎች ላይ የመወያየትና የመሳተፍ መብቶች እንደሚጥስ የህግ ባለሙያዎች ያስረዳሉ።
በተለይ ካለፈዉ ሚያዚያ ጀምሮ እየተካሄደ ያለዉ ተቀዉሞ የብዙ ሰዉ ህይወት ጠፍቷል፣ ንብረትም ወድሞዋል። መንግስትም የተቀናጀውን የጋራ ማስተር ፕላን የሚከታተለዉ መሥሪያ ቤት መታገዱን እና ፕላኑም ያለ ህዝብ ፍላጎት እንዳይተገብር ማገዱን ባለሥልጣናቱ አስታዉቀዋል።መንግሥት ከዚሕም በተጨማሪ ባሁኑ ሰዓት በተለያዩ ቦታዎች ህዝብን ማወያየት ጀምሪያለሁ ቢልም መንግስት የማወያየት ባህሉ ለየት ያለ መሆኑን የህግ ባለሙያ የሆኑት ዶክተር ፄጋዬ ራጋሳ ያሰረዳሉ፣ <<ይኸ ህዝቡ ጋር ዉይይት ማለት በኢሕአዴግ አሰራር ህዝቡን ማሳመን ሳይሆን እንዲቀበል ማስገደድ ማለት ነዉ። እግረ መንገዱን ደግሞ በዉይይቱ ሒደት የተቋዉሞ ሃሳባቸዉን የሚያሰሙትን መለየት እና ከዛ በስዉር በቀን በማታ እየሄዱ ማሰር፣ ማስጠቆም፣ መጠቆም፣ እንደዚህ ያለ ነገር እየተካሄደ ነዉ።>>
ይህንን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላንን በተመለከተ የፌድራል መንግስትም ሆነ የኦሮሚያ ምክር ቤት ህዝብን ጠርቶ እንዳለወያየ ትችቶች ቀርቦዋል። ያላወያየበት ምክንያትም አርሶ አደሮችን አፈናቅሎ መሬት ዘረፋ ላይ የተመሰረተ እንቅስቃሴ ለማድርግ ነዉ ሲሉ የተቃዋሚዉ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ (ኦፌኮ) ከፍተኛ አመረሮች ሲተቹት ነበር።ኦፌኮን ጨምሮ ተቋዋሚ ፓርቲዎች ህዝብን ለማወያየት ስበሰባ ሲጠሩ መንግስት የስብሰባ አደረሾች ና ስታድዮሞችን እንዳልፈቀደላቸዉ ይወቅሳሉ።
መንግስት በበኩሉ የተነሳዉን ተቀዉሞዉ ለማርገብ የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላኑን በበላይነት የሚከታተለዉን መሥሪያ ቤት መዝጋቱን አስታዉቋል።ዶክተር ፀጋዬ ግን የመንግሥት መግለጫ ይጠራጠራሉ። <<ማስተር ፕላኑን እናስፈፅማለን ያሉት ሰዎች አሁን ተቋዉሞ ሲነሳ፣ ተቋዉሞዉ የህዝብ ጥያቄ አይደለም ብለዉ ከቆዩ በኋላ ደግሞ የህዝብ ጥያቄ ነዉ፣ ግን እኛ እንሰማለን፣ ነገር ግን ህዝብ እንደለ ሰምተን ከ2006 ጀምሮ አቁመናል፣ ተሰርዞዋል ይላሉ አሁን፣ ለምሳሌ ግን በኦሮሚያ ጨፌ በመጀመርያ ስብሰባ ማስተር ፕላኑን ለመፈፀም የሚያስችል ከአዲስ አበባ ባሻገር በኦሮሚያ ከተሞች ሁሉ፣ በማስተር ፕላኑ ዉስጥ ያሉ የመሬት ነጠቃዎች የሚካሄዱበት መንገድ አዋጅ በማዉጣት፣ ይሕንን እያደረጉ ነዉ፣ እንደዚህ ያለ መንግስት መቼም ታዓማኒነት ሊኖረዉ አይችልም።>>
«መንግስት በሕዝብ ዘንድ አመኔታ ማግኘት ከፈለገ» ይላሉ ዶክተር ፀጋዬ፤ የኦሮሚያ መንግስት አስቸኳይ የምክር ቤት ስብሰባ ጠርቶ ያወጣዉን አዋጅ በገሐድ መሻር አለበት።ማስተር ፕላኑ ተሰርዟል የሚሉ ከሆነም በምክር ቤት ደረጃ ተወያይቶ በአደባባይ መሰረዙን መናገር እንዳለባቸዉ፣ ለጠፋዉ ህይወት እና ንብረት ሐላፊነት መዉስድ እንዳለባቸዉም ዶክተር ፀጋዬ ያብራራሉ። ይህም የመንግስት ባለስልጣናት ስራ መልቀቅ ጀምሮ በግድያ የተሳተፉ ወታደሮችን በህግ ማስቀጣት ድረስ ይሄዳል ሲሉ ዶክተር ፀጋዬ ለዶቼ ቬሌ ተናግሮዋል። ይሁን እንጂ ይላሉ፣ << እኔ ደግሞ እሄ ይሆናል ብዬ አላምንም፣ ኢሕዴግን አዉቃለሁ፣ እነዚህ ሰዎች ፣ ጥሩ በመስራት በሕዝብ ዘንድ አሜኔታ የማግኘት ልማድ የላቸዉም። ያላቸዉ ነገር ህዝብን ሰብስቦ፣ የራሳቸዉን ሃሳብ ተናግረዉ፣ እንዲያምን አድርጎ፣ አላምን ያለዉን ተከታትሎ በአስተዳደራዊ በደል ወይም ደግሞ በሠራዊት እና በደሕንነት መንገድ በማሰር እና በማስፈራራት ከስርዓት ዉጭ ማድረግ ነዉ>>
መርጋ ዮናስ
ነጋሽ መሐመድ