የጠለምት መሬት መንሸራተት ተፈናቃዮች ቅሬታ
ዓርብ፣ የካቲት 21 2017
የጠለምት ተፈናቃዮች ቅሬታ
በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ጠለምት ወረዳ ባለፈው ክረምት በመሬት መንሸራተት የተፈናቀሉ አርሶ አደሮች “የመልሶ መቋቋም ሳይደረግልን አሁንም በችግር ላይ ነን” አሉ። የወረዳው አስተዳደር በበኩሉ ለተፈናቃዮቹ ዘላቂ ሠላም ለማምጣት እየሰራ እንደሆን አመልክቷል።
ነሐሴ 2016 ዓም አጋማሽ በሰሜን ጎንደር ዞን፣ ጠለምት ወረዳ አብና ቀበሌ፣ ልዩ ሥሙ “ኖላ” በተባለ አካባቢ የተፈጠረው የመሬት መንሸራተት በአካባቢው አርሶ አደሮች የሞትና የአካል ጉዳት አድርሷል። በወቅቱ ተፈናቅለው ከነበሩ የአካባቢው ነዋሪዎች መካክል ለዶይቼ ቬሌ አስተያየታቸውን የሰጡ አንድ አርሶ አደር፣ የምግብና የመጠለያ ችግር አጋጥሟቸዋል፣ እንደዚሁም መንግሥት በዘላቂነት አላቋቋመንም በሚል ቅሬታ አሰምተዋል፡፡
ተፈናቃዮቹ የምግብ እርዳታ የሚያገኙት ከህብረተሰቡ ነው
የአብና ቀበሌ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጀጃው ብርሐኑ በበኩላቸው ተፈናቃዮቹ ከፍተኛ የምግብ እጠረት እንዳለባቸው ተናግረዋል፣ እስካሁንም ከህብረተሰቡ በሚደረግ ደጋፍ ነው ህይወታቸውን የሚመሩት ብለዋል። ህብረተሰቡም አሁን እየተሰላቸ በመሆኑ መንግሥት ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።በአማራ ክልል የጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት ጉዳት አደረሰ
የመኖሪያ ድንኳን ለማግኘት ጥረት እየተደረገ ነው
የወረዳው አደጋ መከላከልና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ቡድን መሪ አቶ መሠረት ጥላሁን በሰጡን መረጃ የተፈናቃዮችን የመንኖሪያ ድንኳን በተመለከተ ከአማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት (አመልድ) ጋር በመነጋገር ለመፍታት እየተሰራ ነው ብለዋል፣ የምግብ አቅርቦትን በተመለከት ግን ከታህሳስ 2017 ዓ ም ጀምሮ የለም ነው ያሉት፡፡
“ተፈናቃዮችን በዘላቂነት በሽግሽግ ለማቋቋም እየተሰራ ነው” የወረዳው አስተዳደር
የጠለምት ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጋሻው እንግዳው ተፈናቃዮቹ ያነሷቸው የምግብና የመኖሪያ ድንኳንን በተመለከት ችግር እንደሌለ አመልክተው ተፈናቃዮቹን በዘላቂነት ለማቋቋም ወደ ሌሎች ቀበሌዎች የማሽጋሸግ ሥራ ለመስራት እቀድ ተይዟል ብለዋል፡፡የቀጠለው የመሬት ናዳ ሥጋት በደቡብ
ተጨማሪ መረጃ ከዞኑም ሆነ ከክልሉ አድጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማስተባብሪያ መስሪያ ቤቶች ለማግኘት ያደረግሁት ጥረት አልተሳካም።
ነሐሴ 16/2016 ዓ ም በወረዳው አብና ቀበሌ በጣልው ከባድ ዝናብን ተከትሎ በተፈጠረው የመሬት ናዳ 10 ሠዎች ህይወታቸው አልፏል፣ ከነዚህ መካክል የግማሽያክሉ አስከሬን በናዳው ተዳፍኖ እንደቀረ ነዋሪዎች ተናግረዋል፣ 8 ሠዎች ደግሞ በወቅቱ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ እንሳሣት ሞተዋል፣ 215 ሄክታር መሬትና የእርሻ ማሳ ከነስብሉ ወድሟል፡፡
ዓለምነው መኮንን
አዜብ ታደሰ
ዮሃንስ ገብረግዚአብሔር