1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የጥቅምት 3 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ጥቅምት 3 2018

ለዓለም ዋንጫ እግር ኳስ ጨዋታ ማለፋቸውን ካረጋገጡ የአፍሪቃ አገራት መካከል ጋና አምስተኛ ሁናለች ። ጋና፦ በቀጣዩ የዓለም ዋንጫ ለመሳተፍ አልጀሪያ፣ ግብጽ፣ ሞሮኮ እና ቱኒዝያን ተቀላቅላለች ። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸናፊ ሁነዋል ። የዚህንና የሌሎችን ዝርዝር ከዘገባው ያግኙ ።

ባለፈው ግጥሚያ ሰሜን አየርላንድን 3 ለ1 ነው ያሸነፈው የጀርመን ቡድን ለድሉ ጠንክሮ መሥራት ነበረበት
ባለፈው ግጥሚያ ሰሜን አየርላንድን 3 ለ1 ነው ያሸነፈው የጀርመን ቡድን ለድሉ ጠንክሮ መሥራት ነበረበት፤ ነገርግን የሚፈልገውን ውጤት አግኝቷልምስል፦ Thilo Schmuelgen/REUTERS

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

This browser does not support the audio element.

በዓለም ዋንጫ የእግር ኳስ የመጨረሻ ማጣርያ ጨዋታዎች  ኢትዮጵያ አንዱን አሸንፋ በሌላኛው ተሸንፋ ከምድቡ አምስተኛ ደረጃ አግኝታለች ። የሸገር ደርቢን ጨምሮ የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫን ያስተናገደው የአዲስ አበባ ስታዲየም በምን አይነት ይዞታ ላይ ይገኛል? ጨዋታዎቹን ስታዲየም ገብቶ ከተከታተለ እና የስታዲየሙን ይዞታ ከቃኘ የስፖርት ጋዜጠኛ ጋር ቃለ መጠይቅ ይኖረናል ። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለያዩ ዓለም አቀፍ ፉክክሮች ድል ቀንቷቸዋል ። የጀርመን ቡድን ዛሬ ከሰሜን አየርላንድ ጋር ወሳኝ ጨዋታ ይኖረዋል ። በነገው ዕለት የእንግሊዝ ቡድን በዳውጋቫ ስታዲየም ከላቲቪያ ጋር ይጋጠማል ።

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸናፊ ሁነዋል

ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ሃዊ ፈይሳ እሁድ ዕለት በነበረው የቺካጎ ማራቶን አሸነፈች ። አትሌቷ ያሸነፈችበት 2:14.56 ሰዓት በሴቶች የማራቶን ሩጫ ታሪክ አምስተኛው ፈጣን ተብሎ ተመዝግቧል ። ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት መገርቱ ዓለሙ 2ኛ ደረጃ አግኝታለች፥ የገባችበት ሰአትም 2:17:18 ነው ። የታንዛኒያዋ አትሌት ማግዳሌና ሻውሪ ሦስተኛ ደረጃ ይዛ አጠናቅቃለች ።

በወንዶች ፉክክክር ኡጋንዳዊው አትሌት ጃኮብ ኪፕሊሞ በ2:02:23 አሸንፏል ። ኬንያውያኑ አሞስ ኪፕሩቶ እና አሌክስ ማሳይ ሁለተኛና ሦስተኛ ወጥተዋል ። አሜሪካዊው ኮነር ማንትዝን ተከትለው የገቡት ኢትዮጵያዊያኑ አትሌቶች አትሌት ሁሰዲን መሀመድ እና አትሌት ሰይፉ ቱራ 5ኛ እና 6ኛ ደረጃን አግኝተዋል ።

ዐርብ ዕለት ዩናይትድ ስቴትስ ኒውዮርክ ከተማ ውስጥ በተካሄደው የአትሎስ የአንድ ማይል የቤት ውስጥ እና የጎዳና ውድድር ኬንያዊቷ አትሌት ፌዝ ኬፕዬጎን በ4:17.78 በሆነ ጊዜ አሸንፋለች ። የኦሎምፒክ የሦስት ጊዜያት አሸናፊዋ እና በዓለም ፉክክር የአምስት ጊዜያት ባለድሏ ኬኒያዊት አትሌት በኬንያ ሽልንግ ሲመነዘር 7.7 ሚሊዮን አግኝታለች ። $60,000 ዶላር ማለት ነው ። ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃ ያገኙ ሯጮች እያንዳንዳቸው 25,000 ዶላር ተሸልመዋል ።

በአትሎስ የአንድ ማይልስ ፉክክር ሁለተኛ የወጣችው ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ ፤ ፎቶ፥ ከማኅደርምስል፦ Vincent Thian/AP/picture alliance

በዚህ ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ (4:19.75 ) ሁለተኛ ወጥታለች ። ሌላኛዋ የአገሯ ልጅ አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ በበኩሏ 4:33.20 በመግባት 4ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቅቃለች ። አሜሪካዊቷ ኒኪ ሒልትዝ ሦስተኛ ደረጃ አግኝታለች ። አራተኛ፣ አምስተኛ እና ስድስተኛ ደረጃ ያገኙ ሯጮችም የገንዘብ ሽልማቱ ተቋዳሾች መሆናቸው ተዘግቧል ። ለአራተኛ ደረጃ 8,000 ለአምስተኛ 5,000 እንዲሁም ለስድስተኛ 2,500 ዶላር የገንዘብ ሽልማት መሰጠቱም ታውቋል ። ተፎካካሪዎች በውድድሩ ወቅት የኣትሎስ (Athlos) ማለትም በግሪክኛ «ፉክክር» የሚል ስም ያለበት መለያ ይለብሳሉ ።

የዓለም ዋንጫ ማጣርያ የእግር ኳስ ጨዋታዎች

ለዓለም ዋንጫ እግር ኳስ ጨዋታ ማለፋቸውን ካረጋገጡ የአፍሪቃ አገራት መካከል ጋና አምስተኛ ሁናለች ። ከ15 ዓመታት በፊት የዓለም ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ ላይ መድረስ የተሳካላት ጋና፦ በቀጣዩ የዓለም ዋንጫ ለመሳተፍ አልጀሪያ፣ ግብጽ፣ ሞሮኮ እና ቱኒዝያን ተቀላቅላለች ። የሚቀጥለው የዓለም ዋንጫ የሚካሄው በዩናይትድ ስቴትስ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ የጋራ አዘጋጅነት ነው ።  ጋና በምድቡ ከኮሞሮስ ጋር በነበራት የመጨረሻ ግጥሚያ ለማለፍ የሚጠበቅባት አንድ ነጥብ ማግኘት ብቻ ነበር ። አክራ ስፖርት ስታዲየም ውስጥ በነበረው ግጥሚያ ግን አንድ ለዜሮ ድል አድርጋ ማለፍ ችላለች ። ሁለተኛ ደረጃ ላይ ትገኝ የነበረችው ማዳጋስካር በማሊ 4 ለ1 በመሸነፏ ደግሞ ጭራሽ ጋና ለማለፍ ምንም አይጠበቅባትም ነበር ።  

በዘጠኝ ምድብ ስድስት ስድስት ተጋጣሚዎችን በማካተት ከተደለደሉት አምሳ አራት አገራት መካከል ከየምድባቸው በነጥብ አንደኛ የሆኑት በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ተፎካካሪነት ያልፋሉ ። ከአጠቃላዩ ምድብ ጥሩ ነጥብ የሰበሰቡ አራት ሌሎች ቡድኖችም ግማሽ ፍጻሜ እና የፍጻሜ ውድድር አድርገው አሸናፊው ይለያል ። ከዚያም አፍሪቃን የሚወክል ዐሥረኛ ቡድን ለመሆን ከእሥያ፣ ከደቡብ አሜሪካ፣ ከኦሺያና እንዲሁም ከመካከለኛው አሜሪካ እና የካሪቢያን እግር ኳስ ማኅበር ኮንፌዴሬሽን (CONCACAF)በደርሶ መልስ ይጋጠማል ማለት ነው ።

የአፍሪቃ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ዓርማ

ኤርትራ ከውድድሩ ከወጣች በኋላ ካፍ ባወጣው መግለጫ መሠረት ዘንድሮ ከየምድባቸው መጨረሻ ከወጡ ቡድኖች ጋር የተደረጉ ነጥቦች እንደሚቀነሱ ጠቅሷል ። በዚህም መሠረት ከየምድቡ የመጨረሻ ደረጃ የሚገኙ ቡድኖችን ያሸነፉ እና ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ቡድኖች ላይ ተጽእኖው ከበድ ይላል ።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ2026 የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ጨዋታዎቹን ከጊኒ ቢሳው እና ቡርኪና ፋሶ አድርጓል ። ብሔራዊ ቡድኑ በቡርኪናፋሶ ትናንት የ3 ለ1 ሽንፈት ደርሶበታል ።  ባለፈው ረቡዕ በነበረው ግጥሚያ ጊኒ ቢሳውን በራምኬል ጀምስ (27') ብቸኛ ግብ 1-0 ማሸነፍ ችሏል ። ከምድቡ አንድ ነጥብ ብቻ ያላት ጅቡቲን ብቻ ቀድሞ በ9 ነጥብ በአምስተኛነት አጠናቅቋል ። ቡርኪናፋሱ ከግብጽ በአምስት ነጥብ ተበልጣ በ21 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ።

የአዲስ አበባ ከተማ እግር ኳስ ፍጻሜ ጨዋታ

19ኛው የአዲስ አበባ ከተማ እግር ኳስ ሕዳሴ ዋንጫ አዲስ አበባ ስታዲየም ውስጥ ትናንት በደማቅ ሁኔታ ተከናውኗል ።  በፍፃሜ ጨዋታው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከመቻል ጋር ተጋጥሞ 2 ለ1 አሸንፏል ። ቅዱስ ጊዮርጊስ (ሳንጃው) ከቡድኖች ሁሉ የበላይ በመሆንም የዘንድሮውን ዋንጫ ወስዷል ። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የፀባይ ዋንጫ ተሸልሟል ።

ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን አላሟላም በሚል ውድድሮችን እንዳያካሂድ በፊፋ የታገደው የአዲስ አበባ ስታዲየም ከረዥም ጊዜ በኋላ ነበር የአገር ውስጥ ውድድሮችን እንኳን ያስተናገደው ። ስታዲየሙ ለረዥም ጊዜ የተለያዩ እድሳቶች ሲደረጉበት ነበር ። ለመሆኑ የመጫወቻ ሜዳው እና የታዳሚያን መቀመጫዎች በአሁኑ ወቅት ምን ማሻሻያ ተደረገላቸው ።  የኢትዮኤፍ ኤም 107.8 ኢትዮ ስፖርት አዘጋጅ እና አቅራቢ ምሥጋናው ታደሰ የትናንቱን ግጥሚያ አዲስ አበባ ስታዲየም ታድሞ ተከታትሏል ።

በካታንጋ በኩል መቀመጫዎቹ ከፊት ካሉት ጋር የተቀራረቡ በመሆናቸው ጉልበት ለመዘርጋት ያስቸግራሉ የሚሉ ቅሬታዎች ተደምጠው ነበር ። አንተ ስታዲየሙን ስትመለከት ምን ታዘብህ አንተ ባልነበርክበት አቅጣጫስ ከነበሩ ሰዎች የተሰሙ ቅሬታዎችን ለማጣራት ሞክረሀል? 

በዓለም ዋንጫ ማጣርያ የእግር ኳስ ጨዋታዎች ባለፈው ዐርብ ሉክዘምበርግን 4 ለ0 ድል ያደረገው የጀርመን ቡድን ምስል፦ Kai Pfaffenbach/REUTERS

ባለፈው ዐርብ ሉክዘምበርግን 4 ለ0 ድል ያደረገው የጀርመን ቡድን ዛሬ ማታ ከሰሜን አየርላንድ ጋር ይጋጠማል ።  በመጀመሪያ ግጥሚያው ሰሜን አየርላንድን 3 ለ1 ነው ያሸነፈው ። የፊታችን ዐርብ ደግሞ ከሉግዘምበርግ ጋር የመልስስ ጨዋታ ይጠብቀዋል ። በመቀጠል ከአንድ ወር በኋላ ከስሎቫኪያ ጋር የመልስ ግጥሚያ ያደርጋል ። ቡድኑ በስሎቫኪያ 2 ለ0 መሸነፉ የሚታወቅ ነው ። 

ዛሬ ማታ፦ ስሎቫኪያ ከሉግዘምበርግ፣ ስሎቬኒያ ከስዊትዘርላንድ፣ ስዊድን ከኮሶቮ፤ አይስላንድ ከፈረንሳይ፣ ዩክሬን ከአዘርባጃን እንዲሁም ዌልስ ከቤልጂየም ጋር ይጋጠማሉ ።  ትናንት ግሪክን 3 ለ1 የያሸነፈችው ዴንማርክ እስካሁን የሚያሸንፋት ጠፍቶ ከምድቧ በ10 ነጥብ የበላይ ሁናለች ። ትናንት ቤላሩስን 2 ለ1 ድል ያደረገችው ስኮትላንድ ትከተላለች ።

በነገው ዕለት ደግሞ፦ የእንግሊዝ ቡድን በዳውጋቫ ስታዲየም ከላቲቪያ ጋር ይጋጠማል ። የእንግሊዝ ቡድን በሐሙስ ግጥሚያ ዌልስን 3 ለ0 ማሸነፉ ይታወቃል ። ቱርክ ከጆርጂያ፣ ስፔን ከቡልጋሪያ፣ የአየርላንድ ሪፐብሊክ ከአርሜኒያ፣ ፖርቹጋል ከሐንጋሪ፣ ጣሊያን ከእሥራኤል እንዲሁም አንዶራ ከሠርቢያ የሚጋጠሙት ነገ ነው ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ታምራት ዲንሳ

 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW