1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የፓስፖርት አሰጣጥ ላይ የሚነሱ ቅሬታዎች

ዓርብ፣ ሐምሌ 26 2016

ከፓስፖርት አሰጣጥ ጋር በተገናኘ «በትግራይ ተወላጆች ላይ ከፍተኛ የሆነ እንግልት፣ ወከባ እና ማስፈራራት እየደረሳቸው ስለመሆኑ በምርመራ ለማረጋገጥ ችያለሁ» ሲል ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ የተባለው ሲቪክ ድርጅት ገለፀ።

የኢትዮጵያ ፓስፖርት
የኢትዮጵያ ፓስፖርት ፎቶ፤ ከማኅደር ምስል DW/S. Wegayehu

የፓስፖርት አሰጣጥ ላይ የሚነሱ ቅሬታዎች

This browser does not support the audio element.

ከፓስፖርት አሰጣጥ ጋር በተገናኘ «በትግራይ ተወላጆች ላይ ከፍተኛ የሆነ እንግልት፣ ወከባ እና ማስፈራራት እየደረሳቸው ስለመሆኑ በምርመራ ለማረጋገጥ ችያለሁ» ሲል ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ የተባለው ሲቪክ ድርጅት ገለፀ። የኢምግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊት ዓመታዊ የሥራ ክንውናቸውን የተመለከተ መግለጫ በሰጡበት ወቅት መሰል መጉላላት ደረሰብኝ ካለ ጋዜጠኛ ጥያቄ ቀርቦላቸው የነበረ ሲሆን «ከድንበር አካባቢ የሚመጡ ሰዎች ይህንን ቅሬታ ያቀርባሉ» ብለዋል። 

በክልሉ የሚሰጠው የመታወቂያ እና የመሳሰሉ ነገሮች ጋር በተገናኘ ሥራ የሚፈልጉ ጉዳዮች ስለሆኑ ችግሮች ሊኖሩ እንደሚችሉ አመልክተው፣ ሆኖም አስፈላጊ ማስረጃ እስካቀረቡ ድረስ የመስተናገድ መብታቸው የተጠበቀ ነው ብለው ነበር።

ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ የትግራይ ተወላጆች በስማቸው ምክንያት «ኤርትራዊ ነህ አይገባህም» በሚሉ እና ሊገኙ የማይችሉ የሩቅ ዘመድ መታወቂያዎችን በመጠየቅ ፓስፓርት ለማግኘት የቀጠሮ ጊዜያቸውን ጠብቀው የሚሄዱ ሰዎች ለእንግልት እንደሚዳረጉ መገንዘቡን አመልክቷል።

ድርጅቱ በተለያዩ ቀናት የፓስፖርት አሰጣጡ ምን ይመስላል የሚለውን በዋናው መሥሪያ ቤት በመገኘት መመልከቱን ገልጾ ፓስፖርት ለመውሰድ ከትግራይ ክልል የመጡ እንዲሁም በአዲስ አበባ የሚገኙ የትግራይ ተወላጆች እንግልትን ጨምሮ ለወከባ መዳረጋቸውን ከ20 በላይ ተገልጋዮችን በማነጋገር ማረጋገጡን ጠቅሷል።

በፍትህ ሚኒስቴር ውስጥ ዐቃቤ ሕግ ሆነው በመሥራት ላይ የሚገኙ ሰው «አንተ ኤርትራዊ ነህ ስለዚህ የኢትዮጵያ ፓስፖርት አይገባህም» ተብለው እንደነበርና ይህ ሪፖርት ከመውጣቱ በፊት «ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ» ፓስፖርት ማግኘታቸውን እንዲሁም አዲስ አበባ መኖር ከጀመሩ ከ33 ዓመታት በላይ የሆናቸው ሰው ካናዳ የሚገኙ ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ ይህንኑ አገልግሎት ለማግኘት ቢሄዱም የወላጆቻቸውን መታወቂያ እንዲያመጡ ተጠይቀው በሕይወት እንደሌሉ ቢገልፁም፣ የሌላ ዘመድ መታወቂያ እንዲያቀርቡ መጠየቃቸውን ድርጅቱ አመልክቷል።

ከፓስፖርት አሰጣጥ ጋር በተገናኘ «በትግራይ ተወላጆች ላይ ከፍተኛ የሆነ እንግልት፣ ወከባ እና ማስፈራራት እየደረሳቸው ስለመሆኑ በምርመራ ለማረጋገጥ ችያለሁ» ሲል ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ የተባለው ሲቪክ ድርጅት ገለፀ። ፎቶ ከማኅደር ምስል Solomon Muche/DW

የኢምግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊት የተቋሙን ዓመታዊ የሥራ ክንውን የተመለከተ መግለጫ በሰጡበት ወቅት፣ መሰል መጉላላት ደረሰብኝ ካለ አንድ ጋዜጠኛ ጥያቄ ቀርቦላቸው የነበረ ሲሆን «ከድንበር አካባቢ የሚመጡ ሰዎች ይህንን ቅሬታ ያቀርባሉ» ብለዋል። 

ኃላፊዋ አክለው እንዳሉት ማንኛውም ሰው አስፈላጊ ማስረጃ እስካቀረበ ድረስ ግን የመስተናገድ መብቱ የተጠበቀ ነው ሲሉ ምላሽ ሰጥተው ነበር።

ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች ኢትዮጵያ ቅሬታ የቀረበበት ተቋም በኢትዮጵያ የሚገኙ ሌሎች ፓስፖርት ፈላጊዎች እና የትግራይ ተወላጆች ላይ «ፓስፖርት ለማግኘት እጅግ የተለያዩ እና የተራራቁ» ያላቸውን አሠራሮች እየተከተለ ይገኛል በማለት «የዜጎች እኩልነት እና የመዘዋወር መብት» እንዲከበር ጠይቋል።

በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ ሰፊ ማሻሻያ እና ለውጥ እያደረገ እንደሚገኝ የገለፀው የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ችግሮች በሂደት እየተስተካከሉ እንደሚሄዱ ባለፈው አንድ ዓመት አከናወንኩት ያለው የለውጥ ሥራ ማሳያ መሆኑን ይጠቅሳል። ተቋሙ ላለፉት 30 ዓመታት ከሀገር ለመውጣትም ይሁን ከውጭ ወደ ውስጥ ለመግባት «እግድ» ተጥሎባቸው የነበሩ የተባሉ 10 ሺህ ሰዎች ከእግድ ነፃ መደረጋቸውን በቅርቡ አስታውቆ ነበር።

ሰሎሞን ሙጬ 

ሸዋዬ ለገሠ

አዜብ ታደሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW