የሰባተኛው የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ ሂደት በፖለቲካ ተንታኞች እይታ
ዓርብ፣ ግንቦት 21 2018
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ እንዳስታወቀው የፊታችን ሰኞ ግንቦት 24 ቀን፣ 2018 ዓ.ም በሚካሄደው የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ 42 የፖለቲካ ድርጅቶች ይወዳደራሉ። ስለ ምርጫው ሂደት ዶቼቬለ ምልከታቸውን ከጠየቃቸው ተንታኞች አንዱ ዶክተር ሙከረም ሚፍታሕ- በሲቪል ሠርቪስ ዩኒቨርስቲ ረዳት ፕሮፌሰርና የፖሊስ ጉዳይ አጥኚ ካለፈው ምርጫ ጋር በማነጻጸር በምርጫው ሂደት ከተወዳዳሪ ፓርቲዎች በኩል ታይተዋል ያሏቸውን ድክመቶች አስረድተዋል።ዶክተር ሙከረም እንዳሉት በአሁኑ ምርጫ ቀድሞ ከነበሩት ምርጫዎች በተለየ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጠንከር ያለ የፖለቲካ አቅጣጫ የያዘ ፖሊሲ አላማቅረባቸውን ታዝበዋል።የምረጡኝ ቅስቀሳዎቻቸውም ኅብrt,ሰቡን የሚያሳስቡ መሠረታዊ አጀንዳዎች ላይ ብዙም ትኩረት አልሰጡም።
ሌላው ዶቼቬለ ያነጋገራቸው የኢትዮጵያ እና የአፍሪቃ ቀንድ የፖለቲካ ጉዳዮች ተንታኝ አቶ መስፍን አማን የአሁኑን የምርጫ ሂደት ካባለፈው ጋር በማነጻጸር በአሁኑ ከባለፈው ለየት ያሉ ያሏቸውን ሁኔታዎች ሲገልጹ «ቀደም ባሉት ጊዜያት ምርጫው ሲቃረብ ፖለቲካው ሞቅ ይል እንደነበር አስታውሰው አሁን ግን መቀዛቀዝና ውዝግብ እንደታየ»ተናግረዋል። ገዥው ፓርቲ ምርጫው መካሄድ አለበት በሚለው ሀሳቡ መጽናቱን ተቃዋሚ ፓርታዎች ደግሞ በርሳቸው እይታ በግምሽ ልብ ወደ ምርጫ መግባታቸው ታይቷል ብለዋል።
ዶክተር ሙከረም ሚፍታህ በበኩላቸው ልሂቃን ለምርጫው ትኩረት አለመስጠታቸው ሌላው በአሁኑ ምርጫ ሂደት የታዘቡት ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። ይህም ከስርዓቱ ጋር የተያያዙ እንቅስቃሴዎች ካልሆኑ በስተቀር ጉዳዩ እንደ አጀንዳም ተነስቶ አያውቅም ያሉት ዶክተር ሙከረም ይህም ከምርጫው ጋር ተያይዞ መሠረታዊ ለውጥ አለመጠበቅ መሆኑን እንደሚያመለክት ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ እንዳለው ከ50 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ለመምረጥ ተመዝግቧል። ይህም እስከዛሬ በኢትዮጵያ በተካሄዱት ምርጫዎች ለመምረጥ ከተመዘገበው ህዝብ ቁጥር ከፍተኛው መሆኑ ተነግሯል። ምንም እንኳን ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ ለመምረጥ ቢመዘገብም ለምርጫውያለው ጉጉትም ሆነ ስሜት ከባለፈው ምርጫ ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ መሆኑ ይሰማል። አቶ መስፍን እንደገለጹት «ይህ የሚያመለክተው ብመርጥ በምርጫ ካርዴ ሁኔታዎችን ማሻሻል አልችልም ብሎ ሰዉ ተስፋ የቆረጠ ነው የሚመስለው ።ያለው ስሜት ብመርጥም ምንም አይቀርብኝም የሚል ዓይነት መሆኑን ገልጸው ይህም አደገኛ አዝማሚያ መሆኑን አስረድተዋል።
የፊታችን ሰኞ በትግራይ ክልል ሙሉ በሙሉ ማለትም በ38 ምርጫ ክልሎች እንዲሁም በአማራ ክልል በ8 ምርጫ ክልሎች ምርጫ እንደማይደረግ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል። #ምርጫ2018 #EthiopiaElection2026
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ