1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የ2ቱ ሱዳን መንግሥታት ውዝግብና የኑባ ብሔረሰብ ችግር

ረቡዕ፣ ነሐሴ 2 2004

ደቡብ ሱዳንን ከሱዳን ጋ በሚያዋስነው ድንበር አካባቢ የሚኖሩት የሱዳን ዜጎች የሆኑት የኑባ ብሔረሰብ አባላት ተቀናቃኞቹ ሁለቱ ጎረቤት ሀገራት ስምምነት የሚደርሱበትን ዕለት በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።

A soldier of South Sudan's SPLA army holds his rifle near an oil field in Unity State April 22, 2012. REUTERS/Goran Tomasevic (SOUTH SUDAN - Tags: MILITARY CIVIL UNREST) Die Sudanesische Volksbefreiungsbewegung (englisch Sudan People’s Liberation Movement, abgekürzt SPLM; arabisch ‏الحركة الشعبية لتحرير السودان‎) ist eine politische Partei und ehemalige Widerstandsbewegung im Sudan und im Südsudan.
ምስል Reuters

ኑባውያኑ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን ተገንጥላ ነፃ ሀገር ከሆነች ወዲህ በሁለቱ ሀገራት ቀጠለው ውዝግብ አሁንም ትልቅ ችግር ውስጥ ናቸው። ለኑባ ብሔረሰብ ርዳታ ያቀርቡ የነበሩት ብዙዎቹ ድርጅቶችም በውዝግቡ የተነሳ አካባቢውን ለቀው የወጡበት ድርጊትም ችግራቸውን አባብሶታል።
ኑባውያኑ ምንም እንኳን ራሳቸውን እንደ ደቡብ ሱዳናውያን ቢመለከቱም፡ ከነፃነቱ በኋላ ግዛታቸው ከሱዳን ጋ እንደተጠቃለለ እንዲቆይ ተወስኖዋል። ውሳኔውን የተቃወሙት በምሕፃሩ ኤስ ፒኤልኤም - ሰሜን ብሎ ራሱን የሚጠራው የሱዳን ነፃ አውጪ ንቅናቄ ዓማፅያን አካባቢውን በመቆጣጠራቸው አካባቢው፡ ብሎም ያካባቢው ነዋሪዎች ኑባውያን የሱዳን መንግሥት በተደጋጋሚ በ ሚግ 29 በሚያካሂደው የቦምብ ጥቃት ዒላማ ሆነዋል። እንደሚታወቀው ካለፈው ሰኔ ወር መጀመሪያ ወዲህ በኑባ ተራሮች ውጊያ እንደገና ተጀምሮዋል። በዚሁ አካባቢ በሚገኘው የጊደል ቀበሌ ዓማፅያኑ ያቋቋሙት መንግሥት ተጠሪ የሆኑት ባራባስ ኩኩ ያካባቢው ሕዝብ ስጋት ምን ያህል ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል።
« አንዳንድ የሕዝቡን ችግር ለማቃለል እየሞከርኩ ነው። ብዙዎች በደቡብ ሱዳን ድንበር ወደሚገኘው ይዳ መሸሽ ይፈልጋሉ፤ ሌሎች ራቅ ብለው ወደ ደቡቡ ወይም ወደ ኬንያ ወይም ወደሌላ ቦታ መሄድ ይፈልጋሉ። »
የሱዳን ተዋጊ ጄቶች በሚያካሂዱት ጥቃት አዘውትሮ ሰለባ የሚሆነው፡ ከብቶቻቸውን የሚጠብቁ ወይም ውኃ ሊቀዱ የሚወጡ ሲቭሎች፡ እንዲሁም፡ ሴቶችና ሕፃናት ጭምር ናቸው። ወንዶችና ሴቶችም በተደጋጋሚ በሚጣሉ የቦምብ ድብደባ የመቁሰል ወይም የመገደል ዕጣ ስለሚገጥማቸው ብዙዎች ማሳዎቻቸውን ለማረስ መውጣት እንኳን ይፈራሉ። በዚህም የተነሳ፡ ያካባቢው ሕዝብ የረሀብ አደጋ ደርሶበታል፤ የሰብዓዊ ርዳታ እንዳያቀርቡለት ደግሞ የሱዳን ፕሬዚደንት ኦማር ሀሰን ኧል በሺር ከሰሜን ሱዳን ወደ ኑባ ተራሮች የሚወስደውን ብቸኛውን መንገድ ዘግተዋል። ከዚህ በተረፈ ባካባቢው የሚንቀሳቀሱት ብዙዎቹ ዓለም አቀፍ የርዳታ ድርጅቶች የቦምቡን ጥቃት በመሸሽ አካባቢውን ለቀው ወጥተዋል። ሰብዓዊ ርዳታ የሚያቀርቡት በሱዳን የሰሜን ኮርዶፋን ክፍለ ሀገር ርዕሰ ከተማ ኤል ኦቤይድ የቀሩት የካቶሊካዊቱ ቤተክርስትያን ቡድን ቀሳውስት እና መነኮሳት ብቻ ናቸው። ቡድኑ በጊደል አንድ ሐኪም ቤት ከፍተዋል። ሰማንያ አልጋ ብቻ እንዲይዝ የተገነባው ሐኪም ቤት በአሁኑ ጊዜ ሦስት መቶ ሕሙማንን ያክማል። ብዙዎቹ ልክ እንደ የሀያ ሁለት ዓመቷ ማልዳ በፊታቸው፡ እጆቻቸውና በእግሮቻቸው ላይ የመቃጠል አደጋ የደረሰባቸው ናቸው።
« በቦምብ ነው የተመታሁት። አይሮፕላኑ ሲመጣ ጎጆዬ ውስጥ ነበርኩ። ከልጆቼ ጋ በጥቃቱ እንዳንጎዳ በሆነ ቦታ ለመሸሸግ ሞክ’ረን ነበር፤ ግን፡ ዘገየን። አምስት ነበርን፡ እኔ ሁለቱን ልጆቼን ይዤ ነበር፤ እና ሌሎች ሁለት ሴቶች አብረውኝ ነበሩ። ልጆቼ እና አንዳ ሴት ወዲያው ሞቱ። »
በሐኪም ቤቱ ለሕሙማኑ አገልግሎት የሚሰጡት ቶም ካቴና የተባሉት የዩኤስ አሜሪካ ዶክተር ተመሳሳይ የመቃጠል አደጋ የደረሰባቸውን በርካታ ሕሙማንን አክመዋል። ካቴና የሱዳን ተዋጊ ጄቶች የሚጥሉት ቦምብ ከመደበኛው የጦር መሣሪያ መደዳ እንደማይቆጠር ነው የሚያምኑት።
« ናፓልም ባይሆንም፡ ከሱ ጋ ተመሳሳይነት ያለው ተጨማሪ ነዳጅ የተቀላቀለበትና ትልቅ ቃጠሎ የሚያስከትል ቦምብ ይመስለኛል። ይህ ነው ሊሆን ይችላል ብየ የማስበው። ምክንያቱም ሰለባዎቹ በጣም ነው የተቃጠሉት። አስከፊ ነው። የሚገርመው ሁሉም ሕሙማን ሁለቱንም እጆቻቸውን፡ ሁለቱን እግሮቻቸውን፡ ፊታቸውን፡ ጀርባቸውን መቃጠላቸው ነው። ሁሉም ተመሳሳይ ጉዳይ የደረሰበት ነው የሚመስለው። »
ብዙ ሲቭሎች እንደተናገሩት፡ ብዙ ያካባቢው ነዋሪዎች የዚሁ በሕዝቡ አንፃር ሽብር ያስፋፋው ውጊያ ሰለባ ሆነዋል።

ምስል DW
ምስል Bettina Rühl

ቤቲና ሩል/አርያም ተክሌ

ሂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW