አሜሪካን የዩክሬን-ሩስያን ጦርነት ለማስቆም ያረቀቀችው የሰላም እቅድና የአውሮጳ ኅብረት አቋም
ረቡዕ፣ ኅዳር 17 2018
መቋጫ ያላገኘው የዩክሬን ሩስያ ጦርነት ከፍፃሜ እንዲደርስ ዩናይትድ ስቴትስ የሰላም እቅድ በሚል ያቀረበችው ሃሳብ ሲያወዛግብ ከርሟል። በእጅጉ ወደ ሩስያ ያመዘነ የተባለው ባለፈው ሳምንት ለዩክሬን የቀረበው የዩናይትድ ስቴትስ ምክረ ሃሳብ ለኪቭ እና ለሌሎች የአውሮጳ ሀገራት የማስጠንቀቂያ ደውል ሆኗል።
ዋሽንግተንና ሞስኮ ያካሄዱትን ንግግር መሠረት ያደረገው በባለ 28 ነጥቡ እቅድ ካካተታቸው ውስጥ ዩክሬን ምሥራቃዊ ግዛቷን ዶንባስን ከዛሬ ሦስት ዓመት ከ9 ወር በፊት ለወረረቻት ለሩስያ እንድትሰጥ ይጠይቃል። እቅዱ የዩክሬን ጦር ሠራዊት ቁጥር በ600 ሺህ እንዲገደብ፣ ዩክሬን የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ድርጅት NATO አባል እንዳትሆን፣ የNATO ወታደሮች ዩክሬን እንዳይገቡ የቀረበው ጥሪ ይገኝበታል።
ሩስያ የምትወጋት ዩክሬንና ደጋፊዋ የአውሮጳ ኅብረት ያልተሳተፉበትን ይህን እቅድ ሩስያን የሚሸልም ሲሉ ተቃውሞአቸውን በማሰማት አማራጭ ያሉትን ማሻሻያ አቅርበዋል። በዚሁ ማሻሻያ የዩክሬን ወታደር ቁጥር በእቅዱ ከቀረበው ከፍ እንዲል፣ የዩክሬን የወደፊት የኔቶ አባልነት ጉዳይ ክፍት ሆኖ እንዲቆይ እና ዩክሬን ለሩስያ አሳልፋ እንድትሰጥ የተጠየቁት መሬቶችን የሚመለከቱት ውይይቶች የተኩስ አቁም ከተደረገ በኋላ እንዲካሄዱ የሚጠይቁ ማሻሻያዎች አቅርበዋል።
ዩናይትድ ስቴትስ የዩክሬን-ሩስያን ጦርነት ለማስቆም ባረቀቀችውና በኋላም የአውሮጳ ኅብረት ያቀረበው ሃሳብ በተካተተበት በተሻሻለው የሰላም እቅድ ላይ የአውሮጳ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ዛሬ መክረዋል። ሚኒስትሮቹ በቪድዮ ባካሄዱት ጉባኤው ላይ ስለተነጋገሩባቸው ዝርዝር ጉዳዮች ፣ ኅብረቱ ለዩክሬን እንዲሰጥ ስለሚፈልገው አውሮጳ በተለይም ቤልጂየም የሚገኘው የሩስያ ገንዘብ ጉዳይና ሾልኮ መውጣቱ የተሰማው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት የዶናልድ ትራምፕ ልዩ መልዕከተኛ የስቲቭ ዊትኮፍ የስልክ ንግግር ጉዳይ ላይ የብራሰልሱን ወኪላችንን ገበያው ንጉሴን በስልክ አነጋግረነዋል።
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ