“ደመወዝ ከተከፈለን 4ኛ ወራችን ነው” የመንዝ ላሎ ምድር ወረዳ ሠራተኞች
ሰኞ፣ ጥር 12 2017
“ደመወዝ ከተከፈለን 4ኛ ወራችን ነው” የመንዝ ላሎ ምድር ወረዳ ሠራተኞች
በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መንዝ ላሎ ምድር ወረዳ የሚገኙ መምህራንና ሌሎች ሠራተኞች “ደመወዝ ከተቀበልን 4ኛ ወራችን በመሆኑ ለከፍተኛ የኢኮኖሚ ችግር ተዳርገናል” አሉ፣ የወረዳው የመንግሥት ኮሚኖኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ችግሩ መኖሩን አረጋግጧል፣ የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ደግሞ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ በጉዳዩ ዙሪያ ጥያቄ ስናነሳ ስልካቸውን ዘግተውብናል።
ደመወዝ በመቋረጡ የተቸገሩ የመንግሥት ሠራተኞች
የወረዳው የመንግስት ሠራተኛ እንደሆኑ የነገሩን አንድ አስተያየት ሰጪ ከጥቅምት 2017 ዓ ም ጀምሮ ደመወዝ ተቋርጧል። ወረዳው ሙሉ በሙሉ በፋኖ ታጣቂዎች ቁጥጥር ስር ከሆነ አንድ ዓመት ቢሞላውም እስከመስከረም 2017 ዓ ም ግን ደመወዝ ከክልል እየተላክ በባንክ ሲከፈላቸው ቢቆይም ባልታወቀ ምክንያት ጥቅምት 2017 ላይ ተቋርጧል ብለዋል።
“ወደ ልመና እየወጣን ነው” ሠራተኞች
ኑሮን መቋቋም ከባድ መሆኑን የሚገልፁት አንድ መምህር፣ ወደ ልመና እየወጣን ነው ሲሉ የችግሩን አሳሳቢነት ገልጠዋል፣ የመንግሥት መስሪያ ቤቶች እስከቅርብ ጊዜ እየሰሩ እንደነበር ጠቁመው አሁን ግን ባለው ችግር ምክንያት ሁሉም እያቆሙ እንደሆነ አብራርተዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ወደ ህክምና ቦታዎች ሄደው ህሙማንን ማሳከም ባለመቻላቸው ህይወት እስከማለፍ ተድርሷል የሚሉት አስተያየት ሰጪዎቹ መድኃኒትም በፀጥታና በመንገድ ችግር ምክንያት ወደ ወረዳው ማስገባት እንዳልተቻለ አመልክተዋል። ብዙዎቹ ሠራተኞች በቀን ሥራ ተሰማርተዋል የሚሉት እኚህ አስተያየት ሰጪ፣ መስራት የማይችሉት ደግሞ በማህበረሰብ ይረዳሉ ብለዋል። ችግሩ እንዲፈታ ምላሽ ለማግኘት ለተለያዩ አካላት ቢደውሉም ምላሽ እንዳላገኙ ነው የሚገልፁት።
ለ4 ወራት ደመወዝ ያልተከፈላቸው 1ሺህ 300 የወረዳው የመንግሥት ሠራተኞች
የመንዝ ላሎ ምድር የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ምንዳ ገበየሁ ችግሩ መኖሩን አረጋግጠዋል፣ በዚህም ምክንያት 1ሺህ 300 የወረዳው የመንግሥት ሠራተኛ በችግር ላይ እንደሆኑ ተናግረዋል። የወረዳውን ዋና አስተዳዳሪ ጭምሮ ብዙዎቹ አመራሮች ወረዳውን ለቅቀው በመሄዳቸው የሠራተኛውን ችግር የሚረዳ አካል በቅርብ የለምም ብለዋል አቶ ምንዳ።
“ህፃናት ወተታቸው ተቋረጠ፣ ወላዶች የሚታረሱበት የለም” ብለዋል፡፡ ጉልበትና ልምድ ያላቸው ሠራተኞች በቀን ሥራ ተሰማርተው በሰብል ስብሰባ ላይ ቢቆዩም አሁን ስራ ባለመኖሩ በሺህ የሚቆጠር ተማሪ ተበትኗል፣ ወደ 700 መምህራንን ጨምሮ 1ሺህ 300 ሠራተኞች ለ4 ወራት ያለደመወዝ መቀመጣቸውን ተናግረዋል።
“ደመውዝ ያገድውን አካል አላውቅም” የሰሜን ሸዋ ዞን መምህራን ማህበር
በአማራ ክልል የሰሜን ሸዋ ዞን መምህራን ማህብር ሰብሳቢ አቶ ችሮታው ካሳዬ፣ የመምህራን ደመወዝ ማን እንዳቋረጠውና ለምን እንደተቋረጠ ባያውቁም “የምመህራን ደመወዝ እንዲከፍል ጥረት እናደርጋለን” ነው ያሉት።
ጉዳዩን በተመለከት ተጨማሪ አስተያየት ለማካተት ለመንዝ ላሎ ምድር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኃይሌ እንግዳሰው ደውለን ሰለተነሳው ቅሬታ እየነገርናቸው እያለ ስልኩን ጆሯችን ላይ ዝግተዋል፣ ደግመን ስንደውል ደግሞ አያነሱም።
ዓለምነው መኮንን
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ