ደቡብ ትግራይ ሞኾኒ ከተማ በተቀሰቀ ግጭት 6 ሰዎች ቆሰሉ
ማክሰኞ፣ ነሐሴ 13 2017
በትግራይ ክልል ደቡባዊ ዞን የተደረገዉ የአስተዳዳሪዎች ሹም ሽር የቀሰቀሰዉ ነዉ በተባለ ግጭት በትንሹ 6 ሰዎች መቁሰላቸዉ ተነገረ።ሰዎቹ የቆሰሉት ሞኾኒ ከተማ ዉስጥ ነዉ። የአካባቢዉ ነዋሪ ታጣቂ ኃይላት አካባቢዉን ለቅቀዉ እንዲወጡ ጠይቋል።በትግራይ ደቡባዊ ዞን ያለው ፖለቲካዊ እና የፀጥታ ስጋት አሁንም ተባብሶ ቀጥሏል። በትላንትናው ዕለት በሞኾኒ ከተማ የትግራይ ሐይሎች አባለት የሆኑ ታጣቂ አንድ የአካባቢው የፀጥታ ዘርፍ ባለስልጣናት ለመያዝ በተባለ በተንቀሳቀሱበት ወቅት፥ ግጭት የተከሰተ ሲሆን በነበረው ቶክስም ቢያንስ በስድስት ሰዎች ላይ ከባድ እና ቀላል ጉዳት መድረሱ ከአካባቢው ነዋሪዎች ሰምተናል።
ያነጋገርናቸው የሞኾኒ ከተማነዋሪዎች እንደገለፁልን፥ ሁነቱ የተከሰተው ከትግራይ ሐይሎች ጋር ልዩነት ውስጥ የገባው፥ በቅፅል ስሙ ቴንሽን ተብሎ የሚታወቅ ኮነሬል ሓለፎም መሓሪ የተባለ የሚሊሻ ሐላፊ ታጣቂዎች በቁጥጥር ስር ለማዋል መሞከራቸው ተከትሎ ነው የተባለ ሲሆን፥ በዚህ መካከል በማህል ከተማ ቶክስ ተከፍቶ ብያንስ ስድስት ሰዎች በጥይት መጎዳታቸው አሰምተናል።
ለዶቼቬለ የተናገሩት የሞኾኒ ከተማ ነዋሪ ሀፍቱ ካሕሳይ፥ ታጣቂዎቹ በማህል ከተማ ቶክስ ከፍተው፥ በርካታ ንፁሃን ላይ ጉዳት አድርሰዋል ብለዋል።
ያነጋገርናቸው የሞኾኒ ሆስፒታል ሐኪም በበኩላቸው፥ ከትላንትና ሁነት በኃላ ስድስት በጥይት የተመቱ ሰዎች ወደ ሆስፒታሉ መምጣታቸው፥ ከእነዚህ መካከል ሁለቱ ከፍተኛ ጉዳት የደረሳቸው በመሆኑ ወደ መቐለ ዓይደር ሪፈራል ሆስፒታል መላካቸው ገልፀውልናል። በሞኾኒ ሆስፒታል ሐኪም የሆኑት ማቸ ፃዲቅ "የጥይት ድምፅ ከሰማን ደቂቃ በኃላ በጥይት የተመጡ ሰዎች በተሽከርካሪዎች ወደሆስፒታላችን መጡ። ብዙ ደም የፈሰሳቸው ነበረ" ብለዋል።
ከዚሁ የትላንት ክስተት በኃላ ዛሬ ሞኾኒ ከተማ በአንፃራዊነት ሰላማዊ ሁኔታ ላይ ብትሆንም፥ እየታየ ያለው ፖለቲካዊ ውጥረት፣ የፀጥታ እና ድህንነት ስጋት በርካቶች ያስቆጣ ሆኖ እንዳለ የከተማዋ ነዋሪ አቶ ሀፍቱ ካሕሳይ ጨምረው ገልፀውልናል።
ከዚህ በፊትም የትግራይ ግዚያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ጀነራል ታደሰ ወረደ የዞኑ ባለስልጣናት ከስልጣናቸው ማውረዳቸው ተከትሎ ተቃውሞዎች የተሰሙ ሲሆን፥ ከቀናት በኃላ ደግሞ ወርደዋል የተባሉት ባለስልጣናት በነበሩበት ስልጣን ስለመቀጠላቸው ተገልጿል።
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
ነጋሽ መሐመድ
ልደት አበበ