1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ደቡብ ኢትዮጵያ እና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ርዕሰ-መስተዳድሮች ተሾመላቸው

ቅዳሜ፣ ነሐሴ 13 2015

አቶ እንዳሻው ጣሰው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልን፤ አቶ ጥላሁን ከበደ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልን እንዲመሩ ዛሬ ቅዳሜ ተሾመዋል። ሹመቱ የተሰጠው የሁለቱ ክልሎች ምክር ቤቶች በአርባ ምንጭ እና በወልቂጤ ባደረጓቸው ጉባኤዎች ላይ ነው። ምክር ቤቶቹ በአዳዲስ የዞን እና የልዩ ወረዳ መዋቅሮችን አጽድቀዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው የተሾሙት አቶ ጥላሁን ከበደ ቃለ መሐላ ሲፈጽሙ
አቶ ጥላሁን ከበደ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው ከተሾሙ በኋላ ቃለ መሐላ ፈጽመዋል። አቶ ጥላሁን ከዚህ ቀደም የገዥው ብልጽግና ፓርቲ የደቡብ ክልል ጽህፈት ቤት ኃላፊ ነበሩምስል SNNPRs Government Communication Affairs Bureau

ደቡብ ኢትዮጵያ እና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ርዕሰ-መስተዳድሮች ተሾመላቸው

This browser does not support the audio element.

12ኛ የፌዴሬሽኑ አካል በመሆን በአዲስ የተዋቀረው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እና የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሚል ራሱን ያደራጀው የቀድሞው የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል በየፊናቸው መሥራች ጉባዔዎቻቸውን አካሄድዋል፡፡ ትናንት ምሥረታቸውን በይፋ ያበሰሩት ክልሎች በዛሬው ውሏቸው የየምክር ቤቶቻቸውን አፈጉባኤዎችና ርዕሳነ መስተዳድሮችን ሲመርጡ ውለዋል፡፡

የሁለቱ ጉባዔዎች ሹመት

ጉባዔውን በወልቂጤ ከተማ ያካሄደው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቀደም ሲል በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን እና በብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አገልግሎት ውስጥ በሃላፊነት ሲሰሩ የነበሩትን አቶ እንዳሻው ጣሰውን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አድርጎ ሾሟል ፡፡ አንዲሁም በአርባምንጭ ከተማ መሥራች ጉባዔውን ያደረገው “ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል” በአንጻሩ የቀድሞው የደቡብ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ጽህፈት ሃላፊ አቶ ጥላሁን ከበደ ክልሉን በርዕሰ መስተዳድርነት እንዲመሩ ሹመት ሰጥቷል።

የደቡብ ክልል ሕዝበ ውሳኔ ውጤት በፌዴሬሽን ም/ቤት ጸደቀ

ሁለቱ ተሾሚዎች ህዝባቸውን በቅንንት ለማገልገል ቃለ መሃላ የፈጸሙ ሲሆን በተለይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል   ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው መልካም አስተዳድርን ጨምሮ ህብረተሰቡ የሚያነሳቸውን አጀንዳዎች በመለየት ምላሽ እንደሚሰጡ ለጉባዔተኛው ተናግረዋል ፡፡

አቶ እንዳሻው ጣሰው የማዕላዊ ኢትዮጵያ ክልልን በምክትል ርዕሰ መተዳድርነት እንዲመሩ ተሾመዋል። አቶ እንዳሻው በሹመት ወደ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከማምራታቸው በፊት በብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አገልግሎት እና በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን በኃላፊነት ሠርተዋል። ምስል SNNPRs Government Communication Affairs Bureau

አዳዲስ መዋቅሮች

የደቡብ ኢትዮጵያ እና የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ተጨማሪ በአዳዲስ የዞንና የልዩ ወረዳ ማዋቅሮችን እንዲደራጁ ውሳኔ አሳልፈዋል። ጉባዔዎቹ መዋቅሮች እንዲደራጁ ውሳኔ ያሳለፉት በአደረጃጀቱ ዙሪያ ለምክር ቤቶቹ የቀረቡ ሞሽኖችን በሙሉ ደምፅ በማጽደቅ ነው ።

በዚህም መሠረት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የም ዞን፣ ምስራቅ ጉራጌ ዞን፣ ጠምባሮ ልዩ ወረዳ፣ ቀቤና ልዩ ወረዳ እና ማረቆ ልዩ ወረዳ ሆነው የአስተዳደር መዋቅራቸው እንዲሻሻል በሞሽኑ ቀርቦ ፀድቋል። 

ለ12ኛ ክልል ሕዝበ ውሳኔ እንዲካኼድ ተወሰነ

በተመሳሳይ የደቡብ ኢትዮጽያ ክልላዊ መንግስት የአማሮ፣የደራሼ፣ የባስኬቶ፣የቡርጂ፣የአሌ፣ልዩ ወረዳዎች እያንዳንዳቸው እራሳቸውን ችለው በዞን ይደራጃሉ።

ከደቡብ ኦሞ ዞን የማሌ፣የሐመር፣የበና ጸማይ፣የሰላማጎ፣የኛንጋቶም የዳሰነች ወረዳ እና የቱርሚ ከተማ አስተዳደር በጋራ በዞን የሚደራጁ ይሆናል።

በሌላ በኩል ከደቡብ ኦሞ ዞን የደቡብ አሪ፣ የወባ አሪ የባካ ዳውላ፣የሰሜን አሪ ወረዳዎች እንዲሁም የጂንካ ከተማ አስተዳደር እና የገሊላ ከተማ አስተዳደር መዋቅሮች በጋራ ሆነው በሌላ ዞን ለማደራጀት የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ አጽድቋል። 

ዳግም የተነሳው የክላስተር ድልደል ቅሬታ

በማዕካላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምሥረታ ላይ የአስፈጻሚ ቢሮዎች ድልድል በዚህኛው ጉባዔ ላይም አከራካሪ መሆኑ አልቀረም፡፡ በተለይም በድልደሉ አንድ የግብርና ቢሮ ብቻ አግኝቷል የተባለው የከምባታ ጠምባሮ ዞን ተወካዮች በጉባዔው ላይ ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡ ከከምባታ ጠንባሮ ዞን መወከላቸውን የጠቀሱት ሁለት የምክር ቤት አባላት “ለየከተሞቹ የተሰጠው የአስፈጻሚ ቢሮዎች ድልድል መሥፈርት በቅድሚያ በዝርዝር ቀርቦ መተማማን መፍጠር ይገባ ነበር ፡፡ የተደለደለበት አግባባም ግልጽ አይደለም “ ብለዋል ፡፡

በአባላቱ ለተነሳው ቅሬታ ምላሽ የሰጡት የቀድሞው የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ርዕስቱ ይርዳው “የተነሳው ቅሬታ ወደፊት ካለው አጠቃላይ ሁኔታ ጋር ተጠንቶ ዳግም በምክር ቤቱ ሊታይ እንደሚችል ታሳቢ ማድረግ ይገባል“ ብለዋል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ የልማት እንቅስቃሴውን ሲመሩ የነበሩ ተቋማት ማሻሻያዎች ተደርጎላቸውና ተስተካክለው እንዲቀጥሉ የተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል ፡፡

በተከታታይ የተካሔዱ ሕዝበ ውሳኔዎች የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል ለአራት እንዲከፈል አድርገውታል። በሕዝበ ውሳኔዎቹ ውጤት መሠረት አራት ክልሎች ተቋቁመዋል። ምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

የክላስተር አዋጭነት እስከምን ድረስ?

አዲስ የተዋቀረው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የዎላይታ ሶዶ ከተማን፤ ራሱን መልሶ ያደራጀው “ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል “ ደግሞ የሆሳዕና ከተማን በርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት መቀመጫነት እንዲያገለግሉ መርጠዋል ፡፡ የተቀሩት ቢሮዎችና ተቋማት ደግሞ በየዞንና ልዩ ወረዳ ከተሞች በክላስተር ተደልድለው አገልግሎት እንዲሰጡ ነው የተደረገው ፡፡ ቢሮዎቹ  ወደ ተለያዩ አካባቢዎች መሄዳቸው ቀደምሲል “ ልማት አላገኘንም  ፣ ትኩረት አልተሰጠንም “ በሚል ሲነሱ የቆዩ ጥያቄዎችን ለመመለስ አንደሚያስችል በማሰብ የተደረገ መሆኑን ክልሎቹ ገልጸዋል።

 ቅሬታ ያስነሳው የክላስተር ከተሞች አደረጃጀት

በምክር ቤቱ አባላት በተነሳው አከራካሪው የክላስተር ድልድል ዙሪያ ዶቼ ቬለ DW አስተያየታቸውን የጠየቃቸው የፖለቲካ ተንታኝና የቀድሞው የተወካዮች ምክር አባል አቶ ዳያሞ ዳሌ የክላስተር አደረጃጀት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ይመልሳል የሚል እምነት አንደሌላቸው ይናገራሉ ፡፡ የተቀላጠፈ አገልግሎት ለማግኘት ጉዳዮችን በአንድ  መሰኮት መጨረስ አሥፈላጊ መሆኑን በምሳሌነት ያነሱት አቶ ዳያሞ “አንድ በእርሻ ዘርፍ ለመሠማራት የፈለገ ባለሀብት ግብርና ቢሮን ለማግኘት ዲላ ፣ ኢንቨስመንት ፍቃድ ለማውጣት አርባ ምንጭ ግብር ለመክፈል ደግሞ ሌላ ከተማ መሄድ ሊጠበቅበት ነው፡፡ ይህ አዋጭ  አይደለም ፡፡ በእኔ እምነተ  መልካ ምድራዊ አቀማመጡ አማካኝ የሆነ አንድ ከተማ በመምረጥ ህብረተሰቡ አገልግሎቱን በአንድ ቦታ የሚያገኝበት ሁኔታ ቢመቻች የተሻለ ይሆናል“ ብለዋል፡፡

ሸዋንግዛው ወጋየሁ

እሸቴ በቀለ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW