ዶክተር አረጋዊ በርሔ አንጋፋ ፖለቲከኛ
ዓርብ፣ መጋቢት 19 2017
በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ በ60ዎቹ የተማሪዎች የለውጥ ንቅናቄ ግንባር ቀደም ተሳታፊ ከነበሩ የወቅቱ ወጣቶች አንዱ ናቸው። ዶክተር አረጋዊ በርሔ። በስልሳዎቹ አጋማሽ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ይማሩ የነበሩ የኤርትራ እና ትግራይ ልጆች የተሰባሰቡበት ማህበረ ገስገስቲ ብሔረ ትግራይ በምህጻሩ ማገብትን መስርተው ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ከነበሩትም አንዱ ናቸው። ከዚያም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርታቸውን አቋርጠው የደርግን መንግሥት በትጥቅ ለመፋለም ወደ ወደ ትውልድ አካባቢያቸው ትግራይ መመለሳቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ዶክተር አረጋዊ ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይን ከመሠረቱ ሰባት ወጣቶች አንዱ መሆናቸውን እራሳቸው የጻፉት የህወሃት የዖለቲካ ታሪክ የተሰኘ መጽሐፍ ላይ ጠቅሰዋል።
በበረሃ የትግል ቆይታቸውም በሲቪልና ወታደራዊ ዘርፍ በመሪነት ተሳትፈዋል። በዚሁ መጽሐፋቸው እንደገለጹት ፓሪቲው ውስጥ በተፈጠረው የርዕዮተ አለም አለመግባባት ከሞት ተርፈው ለስደት ከተዳረጉ ነባር የህወሃት አባላት አንዱ ሆኑ። ከ30 ዓመታት በላይ በዘለቀው የስደት ሕይወታቸው ከፖለቲካ ተሳትፏቸው ጎን ለጎን ያቋረጡትን ትምህርት ገፍተውበት በፖለቲካ ሳይንስ PHD ዲግሪያቸውን ከፍራየ ዑኒቨርሲቴት አምስተርዳም አገኙ። ከስድስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ በህወሃት በሚመራው ኢህአዴግ ላይ የነበረው ባየለው ተቃውሞና ጫና በተከሰተው የመሪ ድርጅት ለውጥ አጋጣሚ በሩ ለተሰደዱ ፖለቲከኞች በመከፈቱ ወደ ሀገር ተመለሱ። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሔራዊ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ሆነውም በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሹመት ተሰጣቸው። በዚያም ላይ የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ትዴፓ) ሊቀመንበር ናቸው።
ሸዋዬ ለገሠ
ፀሐይ ጫኔ