ዶ/ር ነጋሶ በተቃውሞ የፖለቲካ ትግል
ሰኞ፣ ሚያዝያ 21 2011በኦሮሚያ ክልል በቄለም ወለጋ ደምቢዶሎ ከቾ በተባለ ቦታ ጳጉሜ 3 ቀን 1935 ዓ.ም የተወለዱት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጉልህ ሚና ከነበራቸው ግለሰቦች መካከል አንዱ ነበሩ። አምስት አስርት አመታት ገደማ በዘለቀ የፖለቲካ ሕይወታቸው ኢትዮጵያን በፕሬዝዳትነት ከመምራት ባሻገር የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)፣ የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) እና የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ከፍተኛ አመራር ሆነው አገልግለዋል።
ከደርግ ውድቀት በኋላ በ1983 ዓ.ም. ከተማሩበት እና ረጅም ዓመታት ከቆዩበት ጀርመን ሀገር ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ዶ/ር ነጋሶ በሽግግር መንግሥቱ ወቅት የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ እና በኋላም የማስታወቂያ ሚኒስትር ሆነው ሰርተዋል።
ከ1987 እስከ 1994 ዓ.ም. መጀመሪያ ድረስ ኢትዮጵያን በፕሬዘዳንትነት የመሩት ዶ/ር ነጋሶ ከኦህዴድ ኢሕአዴግ አባልነታቸው በገዛ ፈቃዳቸው የለቀቁት በሰኔ 15 ቀን 1993 ዓ.ም. ነው። በግንቦት 1997 ዓ.ም. በተደረገው የኢትዮጵያ ምርጫ በትውልድ ቀያቸው ተወዳድረው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫን አሸንፈዋል። የቀድሞው ፕሬዝዳንት የተወካዮች ምክር ቤት ቆይታ እና ከመንግስት መዋቅር የለቀቁበትን ወቅት ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና መለስ ብለው ያስታውሳሉ። በአንድነት ፓርቲው ውስጥ አብረዋቸው የሰሩት አቶ አስራት ጣሴም ስለ ዶ/ር ነጋሶ የሚሉት አላቸው።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።
ዩሃንስ ገብረ እግዚያብሔር
ተስፋለም ወልደየስ
እሸቴ በቀለ