1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

በሀገሪቱ የምሥራቅ አካባቢዎች ጉዳት ሊያስከትል የሚችል የዝናብ ሁኔታ ማስጠንቀቂያ

መሳይ ተክሉ
ረቡዕ፣ ሰኔ 18 2017

በሀገሪቱ የምሥራቅ አካባቢዎች በተያዘው የክረምት ወቅት ቀጣይ ወራት የከፋ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል የዝናብ ሁኔታ እንደሚጠበቅ የብሔራዊ ሜትሮሎጂ ኢንስቲቲዩት አስታወቀ።

ባለፈው ኅዳር ወር ሕንድ ውስጥ የወረደው ኃይለኛ ዝናብና ማዕበል
ባለፈው ኅዳር ወር ሕንድ ውስጥ የወረደው ኃይለኛ ዝናብና ማዕበል በፎቶ ፎቶ ከማኅደርምስል፦ R.Satish Babu/AFP via Getty Images

ጉዳት ሊያስከትል የሚችል የዝናብ ሁኔታ ማስጠንቀቂያ

This browser does not support the audio element.

 

 ለዶይቼ ቬለ አስተያየታቸውን የሰጡት በኢንስቲቲዩቱ የሶማሌ ክልል እና አጎራባች አካባቢዎች የሜትሮሎጂ ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ዴስክ መሪ አቶ አሸናፊ ሙሉነህ ቀደም ባሉ ዓመታት በድሬደዋ እና ሌሎች ለጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ቀውስ ያስከተሉ የጎርፍ አደጋዎች ዓይነት ሊከሰት እንደሚችል  ትንበያ መኖሩን በመግለፅ አስፈላጊው የቅድም ጥንቃቄ ሥራ መሠራት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

የክረምቱን ወራት የሜትሮሎጂ መረጃዎችን ለዶይቼ ቬለ በስልክ የገለጡት የሶማሌ ክልል እና አጎራባች አካባቢዎች የሜትሮሎጂ ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ዴስክ መሪ አቶ አሸናፊ ሙሉነህ በክረምቱ በምሥራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች የከፋ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል የዝናብ ሁኔታ ሊኖር እንደሚችል የሚጠቁም ትንበያ መኖሩን ገልፀዋል።

«የዘንድሮው ክረምት ከፍተኛ የዝናብ ሁኔታ እና በጎርፍ አደጋ ሳቢያ ከፍተኛ ቀውስ የተመዘገበባቸውን እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር 1998 እና 2010ዓ.ም  የነበሩትን ጊዜያት ይመስላል ተብሎ ይጠበቃል» ብለዋል። 

«ድሬደዋ እና በድሬደዋ ዙርያ እንዲሁም በሰሜን ሶማሌ የጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ የእግር ተዳፋት ፣እንዲሁም ከጭናክሰን እስከ ጅግጅጋ ባሉ የጎርፍ መፋሰሻ መስመሮች ላይ የክረምቱ የከባድ ዝናብ አዝማሚያ ጎርፍንን ያስከትላል። ቀውሶች የሚደገሙበት ሁኔታዎች ሊፈጠሩ ይችላሉ ተብሎ ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያዎች» እየተላለፉ መሆኑን አብራርተዋል።

አቶ አሸናፊ ለጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎችን መሥራት እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል። «በተለይ ለፍርድ ተጋላጭ በሆኑ በድሬደዋ እንዲሁም ወደ ጅግጅጋ አካባቢዎች ቅድመ ማስጠንቀቂያው በተጠናከረ መልኩ ወረዳ ድረስ ተደራሽ በማድረግ ሥራዎችን መሥራት ይጠበቃል»

በድሬደዋ እና አካባቢው በአሁኑ ወቅት እየታየ ስለሚገኘው ከፍተኛ የሆነ የሙቀት ሁኔታ ጥያቄ የቀረበላቸው አቶ አሸናፊ «ከአየር ንብረት ለውጥ እና ከጊዜ ወደ ጊዜ ካለው የአየር ንብረት አለመረጋጋት ጋር ሊያያዝ እንደሚችል» ጠቁመዋል።

መሳይ ተክሉ

ሸዋዬ ለገሠ

ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር

 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW