የግንቦት 20 በዓል በትግራይ ክልል ብቻ
ረቡዕ፣ ግንቦት 20 2017
በኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከሕዝባዊ በዓላት ዝርዝር የተሰረዘው ግንቦት 20 በዓል በትግራይ ክልል ተከብሮ ውሏል ። በዓሉ በሚዘክርበት ስነስርዓት ንግግር ያሰሙት የሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ሊቀመንበር ዶክተር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል፥ ለኤርትራ «እንኳን ለነፃነት ቀን አደረሳችሁ» ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፥ ዕየታየ ነው ያሉት የሰላም ፍላጎት ለማጠናከር ሕወሓት እንደሚሰራ ተናግረዋል ። ሚሊዮን ኃይለሥላሴ ከመቐለ ዝርዝር ዘገባ ልኮልናል ።
ሕወሓት መሩ ኢህአዴግ የደርግ መንግስትን በትጥቅ ትግል የጣለበት ግንቦት 20 በዓል፣ ዘንድሮ ለ34ኛ ጊዜ በትግራይ ክልል እየተከበረ ነው ። ዛሬ ጠዋት በመቐለ ከተማ፤ ሰማእታት ሐወልት ቅጥር ግቢ በተካሄደ ስነስርዓት የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ባለስልጣናት፣ የሕወሓት መሪዎች እና የትግራይ ኃይሎች ወታደራዊ አዛዦች እና ሌሎች በርካቶች የታደሙ ሲሆን፤ በዚሁ ስነስርዓት ንግግር ያሰሙት የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ጀነራል ታደሰ ወረደ የደርግ መንግስትን ለመጣል በተደረገ ትግል ትግሉን ለድል ያበቃችሁ የኢትዮጵያ ሕዝቦች እንኳን ለ34ተኛ ዓመት የድል ቀን አደረሳችሁ ብለዋል ።
ግንቦት 20 በዓል፣ ዘንድሮ ለ34ኛ ጊዜ በትግራይ ክልል ተከብሯል
ጀነራል ታደሰ «በፀረ ደርግ ሕዝባዊ ተጋድሎ፥ የትግራይ ትግል አጋር ሁናችሁ የታገላችሁ እና ደጀን ሁናችሁ ትግሉን ለድል ያበቃችሁ የኢትዮጵያ ሕዝቦች እንኳን ለ34ተኛ ዓመት የደርግ ውድቅ እና የኢትዮጵያ ሕዝቦች ድል አደረሳችሁ፤ አደረሰን የምለው፥ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝቦች የከፈሉት ዋጋ፣ የትግራይ ሕዝብ ደግሞ በተለየ ይህን ድል ለማምጣት ለከፈለው የማይረሳና ያልተመጣጠነ መስዋእትነት ያለኝን ክብር በታላቅ ስሜት እያስታወስኩኝ ነው» ብለዋል።
ባለፈው ዓመት የኢትዮጵያ ፓርላማ አውጥቶት በነበረ የሃይማኖታዊ እና ህዝባዊ በዓላት አዋጅ መሰረት፥ ግንቦት 20 ከሕዝባዊ በዓላት ዝርዝር መሰረዙ የሚታወስ ሲሆን በአንፃሩ በትግራይ ዛሬ ጨምሮ ሰሞኑ ሙሉ ዕለቱ የሚያስታውሱ ስነ ስርዓቶች ሲካሄዱ ሰንብተዋል። በትላንትናው ዕለት በነበረ የግንቦት 20 አከባበር መርሐግብር ንግግር ያደረጉት የህወሓት ሊቀመንበር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል፥ ለኤርትራውያን እንኳን ለነፃነት ቀን አደረሳችሁ ብለዋል።
«የግንቦት 20 ድልን ስንዘክር ከኤርትራ ወንድምና እህቶቻችን ጋር በመሆን...»
ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል "የግንቦት 20 ድልን ስንዘክር ከኤርትራ ወንድምና እህቶቻችን ጋር በመሆን የከፈልነውን መስዋእትነት እናስታውሳለን፥ እናከብራለን። የደርግ ስርዓት በጋራ የታገልን ህዝቦች መሆናችን፣ አቅሞቻችን አስተባብረን ያፈረስነው በመሆኑ፣ በደማችን የጋራ ታሪክ መፃፋችን ይታወሳል። በመሆኑም በዚህ አጋጣሚ ፓርቲያችን ሕወሓት እንኳን ለ34ተኛ ዓመት የነፃነት ቀን አደረሳችሁ የሚል የመልካም ምኞት መልእክት ያስተላልፋል" ሲሉ ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ፦ ዶክተር ደብረፅዮን ሕወሓት ከኤርትራ ጋር ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር እንደሚሠራም ዐሳውቀዋል። ደብረፅዮን «በጦርነቱ ምክንያት በስርዓት መቋጫ ማግኘት የሚገባቸው ጉዳዮች ማየት እንዳለ ሆኖ፥ ከጀኖሳይዳዊ ጦርነቱ በኋላ ዕየታየ ያለው የሰላም ፍላጎት ግን ሊጠናከር እና ስርዓት እንዲይዝ ለማድረግ በእኛ በኩል ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግ ለማረጋገጥ እንወዳለን» ሲሉ አክለዋል።
ሚሊዮን ኃይለሥላሴ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ታምራት ዲንሳ