1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ጦርነት የጎዳቸው የአፋር ክልል ወረዳዎች ለማገገም እየታገሉ ነው

ሰኞ፣ ኅዳር 5 2015

ውጊያ የጎዳቸው የአፋር ክልል ወረዳዎች መረጋጋት ቢጀምሩም የተፈናቀሉ ዜጎቻቸው ወደ ቀያቸው አልተመለሱም። ዶይቼ ቬለ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች እንደሚሉት ባንክ እና ቴሌኮምን የመሳሰሉ መሠረታዊ አገልግሎቶች በቅጡ አይሰሩም። የምግብ እና የመጓጓዣ አገልግሎቶች እጦት እና ቢገኙም የዋጋ መወደድ ለነዋሪዎች ፈተና ሆኗል

Äthiopien Tigray Konflikt Symbolbild
ምስል፦ Eduardo Soteras/AFP/Getty Images

ጦርነት የጎዳቸው የአፋር ክልል ወረዳዎች ለማገገም እየታገሉ ነው

This browser does not support the audio element.

መምህር መሃመድኑር ዑስማን ከሚኖሩበት ሰሜናዊ የአፋር ክልል ዞን ኢረብት ወረዳ በጦርነት ሳቢያ መረጋጋት በተሳነው አከባቢ ከቀዬያቸውና ከመመህርነት የስራ ገበታቸው ከተፈናቀሉ ከሁለት ዓመታት በኋላ አሁን ወደ ስራ ገበታቸው ተመልሰዋል፡፡ መምህሩ አሁን ተገኝቷል ባሉት የሰላም ተስፋ በብዛት በጦርነት ከወደሙት የመማሪያ ክፍሎች መካከል በተረፉቱ በውስኖቹ ውስጥ በዚህ ሳምንት የማስተማር ስራቸውን አንድ ብለው መጀመራቸውንም ይገልጻሉ፡፡ በርግጥ እንደ መምህር መሃመድኑር አስተያየት በጦርነቱ ምክኒያት የተፈናቀለው ማህበረሰብ ሙሉ በሙሉ ወደ ቀዬው አለመመለሱና ከመሰረታዊ ፍላጎቶች መጓደል ጋር ተያይዘው ወደ ትምህርት ገበታቸው የተመለሱ ተማሪዎችም ቁጥር አሽቆልቁሎ መታየቱን አመልክተዋል፡፡ በመሆኑም መሰረታዊ የአገልግሎት አውታሮችን በነዚህ በጦርነት በተጎዱ አከባቢዎች የመመለሱ ስራ ጊዜ የማይሰጠው ነው ይላሉ፡፡ 

"የባንክ አገልግሎት በነዚህ አከባቢዎች ከተቋረጠ 2 ዓመት ደፍኗል" ያሉት እኚው ነዋሪ፤ በኬላዎች ላይ በሚወሰዱ ጥብቅ ቁጥጥሮች መሰረታዊ ፍጆታ እቃዎች አንኳ ወደ እነዚህ አከባቢዎች እንደልብ አለመግባታቸው ኑሮን ፈታኝ አድርጎታል፡፡

የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት እንደ አብዓላ ያሉ የአፋር ክልል ከተሞችን ክፉኛ የጎዳ ነው። ምስል፦ Mariel Müller/DW

በነዚህ በጦርነት ላይ በከረሙ የአፋር ክልል ወረዳዎች አሁን የጦርነት ድምጽ አይሰማም፡፡ በቅርቡ በትግራይ ክልል እና ፌዴራል መንግስት መካከል ተጀመረው የሰላም ሂደትም ተስፋን በማጫሩ ተፈናቃይ ማህበረሰብ ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተሻለ ሁኔታ ወደ ቀዬያቸው መመለስ ጀምረዋል፡፡ 

በሰላሙ ድርድር የአፋር ህዝብ እንደ ሌላው ሁሉ የደስታው ተካፋይ ነው ያሉን ደግሞ የአፋር ሰብዓዊ መብቶች ድርጅት ሊቀመንበር አቶ ገዓዝ አህመድ ናቸው፡፡ እንደ አቶ ገዓዝ ማብራሪያ የአፋር ክልል ሰሜናዊ እና ማዕከላዊ ዞኖች የመሰረታዊ ልማት ዝርጋታዎች ከትግራይ ክልል ጋር የተሳሰሩ መሆናቸው እኩል የችግሩ ገፈት ቀማሽ እንዲሆንም አስገድዷል፡፡ 
የሰብዐዊ መብት ተሟጋቹ ጦርነቱ በአፋር ህዝብ ላይ ያደረሰው ጉዳት ከቁሳዊ ውድመትም በላይ ነው ይላሉ፡፡ “ብዙ ሰዎች በዚህ ጦርነት ህይወታቸው አልፏል፡፡ ከ600 ሺህ የላቁ በስድስቱ ወረዳዎች ብቻ ተፈናቅለው ሰብዓዊ መብታቸውም ክፉኛ ተመሰቃቅሏልም” ነው ያሉት፡፡ 

በጦርነቱ እጅግ የተጎዳው ህዝብ ሰፊ የስነልቦናም ግንባታ የሚያስፈልገውና የአፋር የጦርነቱ ተጎጂ አከባቢዎች ከትግራይና ሌሎችም በጦርነት ከተጎዱ አከባቢዎች እና ማህበረሰብ ጋር ትኩረት የሚያሻቸው መሆኑንም ሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪው አብራርተዋል፡፡ በሰሜን ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመታት የቆየው ጦርነት በሚሊዮን የሚቆጠሩትን ሰዎች አፈናቅሏል፤ በቢሊየን የሚተመኑ ሃብት ንብረቶችን ደግሞ አውድሞ የሺዎችን ህይወትም ቀጥፏል፡፡ 

ሥዩም ጌቱ

እሸቴ በቀለ

ታምራት ዲንሳ
 

ቀጣዩን ክፍል እለፈው የ DW ታላቅ ዘገባ

የ DW ታላቅ ዘገባ

ቀጣዩን ክፍል እለፈው ተጨማሪ መረጃ ከ DW

ተጨማሪ መረጃ ከ DW