ዓርብ፣ ጥቅምት 18 2009
ተቃዉሞዉን ለማብረድም አንዳንድ ማሻሻያዎች አደርጋለሁ ያለዉ መንግሥት ሹምሽር ለማካሄድ እንቅስቃሴ ላይ መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ጌታቸዉ ረዳ ሰሞኑን ተናግረዋል። የፖለቲካ ተቃዋሚዎች ግን ይህ ሕዝቡ ለጠየቀዉ ጥያቄ መልስ አይሆንም ይላሉ። ሥር ነቀል ለዉጥ እንደሚያስፈልግ በማሳሰብም፤ ምርጫ መካሄድ እንደሚኖሩበት ይናገራሉ።
በመድረክ ፓርቲ ዉስጥ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀመንበር የሆኑት ዶክተር መረራ ጉዲና የአስቸኳይ ግዜ አዋጁ ከታወጀ በዋላ በሺዎች የሚቆጠሩ ወደ ጦላይና ዲዴሳ የወታደሮች ማሰልጠኛ ጣቢያዎች እየተወሰዱ እንደሆነ ይገልጻሉ። ሹም ሽሩም ቢሆን «የግለሰብ መለዋወጥ ምንም ፋይዳ የለዉም፣ አገር መሠረታዊ ለዉጥ ትፈልጋለች» ሲሉ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። የሚፈለገዉ የፖሊሲ ለዉጥ መሆኑንም ያመለክታሉ።
ዶክተር መረራ አገሪቱን ወደ ተረጋጋ መልክ ለማምጣት የሽግግር መንግሥት ወይም ባለ አደራ መንግሥት አቋቁሞ ምርጫ መካሄድ እንዳለበት ያሳስባሉ። ይሁን እንጅ መንግሥት ይህን አይቀበልም። አቶ ጌታቸዉ ረዳ ምርጫ የሚካሄደዉ በመደበኛዉ ጊዜ ከአራት ዓመታት በኋላ መሆኑን ተናግረዋል።
«በፓርላማ የተቃዋሚ ፓርቲዎች መቀመጫ የበለጠ እንዲኖር የሚያስፈልገዉን ርምጃ እንወስዳለን። ለዚህም በአገሪቱ በሕጋዊ መንገድ ከሚንሳቀሱት ጋር ተወያይተን የምርጫ ሕጋችን ኪሻሻል ይገባል። ይህም ሕገ መንግሥቱን እንድናሻሻል የሚያስገድድ ከሆነ ጊዜዉ ሲመጣ የምናየዉ ይሆናል። እሱ አይደልም አሁን እየተሠራ ያለዉ። አሁን በሃሳባችን ያለዉ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫዉ አሁን መሆን አለበት፣ ካልሆነ መቸም አይሆንም፤ የሚለዉን ልናስተናግድ አንችልም። ግን እያደረግን ያለነዉ ነገር የምርጫ ዙር መጠበቅ ነዉ። ይህ መንግሥት በአንዴ ተነስቶ ሕግ ቀይሮ ምርጫ ለመጥራት ምንም አላማ የለዉም ። ረጅምና ከባድ ጉዞ አለብን፤ እናም ተቃዋሚዎችም የሂደቱ አካል መሆን አለባቸዉ።»
በዚህ ርዕሰ ጉዳይ የፌስቡክ ከተከታዮቻችንን አወያይተን ነበር። አንዳንዶቹ ገዢዉ ፓርቲ «በምርጫ እንደማይለቅ፣ አስመራጩ ራሱ፣ ቆጣሪው ራሱ፣ ፈራጁ፣ ዳኛው፣ ምስክሩ ራሱ፣ የሚያዋጣው ትግሉን መቀጠል ብቻ እና ብቻነው» ሲሉ፤ ሌሎች ደግሞ «በኔ እምነት አሁን ምርጫ ይደረግ ቢባል „የነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ ነው» የሚሆነው ምርጫ ሲባል መምረጥና መመረጡ ብቻ ሳይሆን አመራረጡና የምርጫው አፈጻጸም ሂደት ነው ወሳኙ» የሚሉ አስተያየታቸዉን ሰንዝረዋል።
መርጋ ዮናስ
ሸዋዬ ለገሠ