28ኛው የሰመርጃም የሙዚቃ ድግስ
ዓርብ፣ ሐምሌ 5 2005የ28ኛው የሰመርጃም የሙዚቃ ድግስ መፈክር « FREE YOUR MIND» «አይምሮህን ነፃ አድርግ» የሚል ነበር። በውሀ በተከበበችው ትንሽ ደሴት ላይ ከ30 000 በላይ ተመልካቾች ተገኝተዋል። ይህ የሬጌን ስልት ብቻ የሚያስኮመኩመዉ የሙዚቃ ድግስ ዘንድሮ የሂፕሆፕ እና ቴክኖ ( ኤሌክትሮ) ባንዶችንም አስተናግዷል። ጥቂቶቹን አርቲስቶች ለመጥቀስ ያህል፣ ሞርገን ሄሪቴጅ፣ ታይረስ ራይሊ፣ ስኑፕ ላይን፣ ታቢለንስ፣ ጀንትልማን እና ፓትሪስ ይገኙበታል።
በድረክ ላይ አርቲስቶቹ እስኪቀያየሩ፤ ሳር ላይ ተቀምጠው ካርታ ሲጫወቱ ካገኘኋቸው ወጣቶች ውስጥ የ20 ዓመቷ ታውሏ ስለ ድግሱ ስትናገር « ከሀምቡርግ ነው የመጣሁት ፤ወደዚህ ስመጣ የመጀመሪያዬ ነው። ድባቡ ፣ አየሩ ደስ ይላል። ውጪ መቀመጥ እንችላለን። ሙዚቃውም ደስ ይላል። ሲፈለግ መደነስ ሲፈለግ መቀመጥ ይቻላል። እሁድ ደግሞ ፓትሪስ ይጫወታል። ያ የበለጠ ያስደስተኛል።» ከሀኖቨር የተጓዘው ዮናስ ደግሞ፦ « ሌላ የሬጌ የሙዚቃ ድግሶች ላይ ተገኝቼ አውቃለሁ። ሰመርጃም ላይ ግን ይህ የመጀመሪያዬ ነው። አሁን የሚቀርበው ሞርገን ሄሪቴጅን ለማየት ጓጉቻለሁ፤ ከዛ ደግሞ ጀንትልማን እና ነገ ማታ ፓትሪስን።
« ቤነ እባላለሁ። ከሀኖቨር ነው የመጣሁት። አንድ ጓደኛዬ መምጣት እንደማትችል ነግራኝ ባጋጣሚ ነው የመጣሁት። በጣም ደስ የሚል ስሜት ነው ያለው። ሰው ሁሉ ዘና ብሏል። ሙዚቃውም በጣም ነው ያስደሰተኝ። ፀሀይዋ ታምራለች። እንዲህ ሆኖ ሊቀጥል ይችላል። በጣም አሪፍ ነው።»
አንዳንዶች በደስታ መንፈስ ሲጨፍሩ ሌሎች በስራ ተወጥረዋል። ካሜሮናዊዋ ወ/ሮ ቴኖሶም ሀገሬ የምናፍቀውን ፀጉር መስራት እዚህ አገኘሁት ይላሉ። « በመጀመሪያ ነገር የአውሮፓ ሴቶች ፀጉራቸው መጎንጎን እንደሞቻል በማመናቸው ደስተኛ ነኝ። ቀደም ሲል አይ ይህ ለአፍሪቃውያን ብቻ ነው፣ ለኛ ፀጉር አይሆንም ይሉ ነበር። አሁን ግን ደንበኞቼ ጀርመናዊያን ፣በአጠቃላይ ነጭ ሴቶች ናቸው። » ከሩሜንያ የመጣችው እና ፀጉሯ እየተጎነጎነ ያለችው አማንዳ፤ እስክትጨርስ ትቁነጠነጣለች፤ « ስሜቱ ደስ ይላል። ፀጉሩ ተሰርቶ እስኪያልቅ ግን በጣም ያማል። ከልጅነቴ ጀምሮ ፀጉሬን በጎንጎን እመኝ ነበር። እሩሜንያ ግን ፀጉሬን እንደዚህ የሚሰራልኝ ሰው አልነበረም።»
የተጎነጎነ ፀጉር፣ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ በየቦታው። ምንም እንኳን ታቢሊንስ ኢትዮጵያ ሩቅ ናት እያለ ቢያቀነቅንም፤ ቅርብ ትመስል ነበር። በሂፕሆፕ ዘፈኑ የሚታወቀው ስኑፕ ዶግ ፤ዘፈኑን ከሬጌ ጋ አስማምቶ በዘንድሮው አመት ስኑፕ ላየን ተብሎ የቀረበበት መድረክ በርካታ ታዳሚዎች ነበሩት። እጇ ላይ ያለፉት 6 አመታት የገባችበትን የክር አምባር ያጠለቀጥው ማሪን ስለሰመርጃም ተሞክሮዋ ፦ « ሙዚቃው ይስበኛል። በርካታ የሬጌ የሙዚቃ ድግሶች ላይ ተገኝቼ ነበር። እዚህ ግን ሰዎች በሙሉ በሰላም ተሰባስበው ስለሚያከብሩ ደስ ይለኛል። ይሁንና ነገሮች ተቀይረዋል። በፊት የምር ነበር አሁን አሁን ግን እዚህ መገኘት የሌለባቸው ባንዶችም ይስተዋላሉ። የሬጌን የሙዚቃ መልዕክት የማያስተላልፉ፤» ማሪ ቴክኖ እና ኤሌክትሮ የሙዚቃ ባንዶችን ማለቷ ነው።
ይሁንና በተመሳሳይ ሰዓት በሁለት ትልቅ መድረኮች ላይ አርቲስቶች ስለተጫወቱ ታዳሚው የሚፈልገውን አርቲስት የመምረጥ እድል ነበረው።
የሶስት ቀኑ የሙዚቃ ድግስ ምን ይመስል እንደነበር ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
ተክሌ የኋላ